Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Thursday, April 26, 2012

ሚስቱን በአሲድ አቃጥሎ ደቡብ ሱዳን ተደብቆ የተያዘው በሞት እንዲቀጣ ተጠየቀ

ሪፓርተር ጋዜጣ
ባለፈው ዓመት ሚያዝያ 30 ቀን 2003 ዓ.ም በልጁ እናት ላይ አንድ ሊትር ሰልፈሪክ አሲድ ደፍቶ ከተሰወረ በኋላ፣ ደቡብ ሱዳን ውስጥ በቁጥጥር ሥር የዋለው ግለሰብና ሁለት ግብረ አበሮቹ በሞት እንዲቀጡ የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ በትናንትናው ዕለት ጠየቀ፡፡ አሲዱ የተደፋባት ግለሰብ በሁለተኛው ቀን መሞቷ ይታወሳል፡፡

 የሟች ወይዘሮ ትዕግሥት መኮንን ባለቤት የነበረው ምናለ አቻም፣ ግብረ አበሮቹ የነበሩት ነበረ ጎሹና ዘለዓለም ውበት የተባሉት ተከሳሾችን ክስ ሲመረምር የቆየው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሦስተኛ ወንጀል ችሎት በሰጠው ፍርድ፣ ሁሉንም ተከሳሾች ጥፋተኛ ብሏቸዋል፡፡ በመሆኑም ዓቃቤ ሕግ እንዲያቀርብ በተጠየቀው የቅጣት ማክበጃ አስተያየት ላይ ሦስቱም ግለሰቦች የፈጸሙት ድርጊት ዘግናኝ፣ ነውረኛና ጨካኝነታቸውን ከማሳየቱም በላይ ድርጊቱን መፈጸማቸውን ያመኑ በመሆኑ ሦስቱም በሞት እንዲቀጡለት ጠይቋል፡፡

የተከሳሾቹ ተከላካይ ጠበቃ ባቀረበው የቅጣት ማቅለያ ቅጣቱ ወደ ዕድሜ ልክ እስራት እንዲቀነስላቸው አመልክቷል፡፡ ፍርድ ቤቱ የግራ ቀኙን የማክበጃና የማቅለያ አስተያየት መርምሮና ከሕጉ ጋር አገናዝቦ የቅጣት ውሳኔ ለመስጠት ለሚያዝያ 22 ቀን 2004 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

ሦስቱም ተከሳሾች ጥፋተኛ በመባላቸው ዓቃቤ ሕግ በሞት እንዲቀጡ የጠየቀበት ወንጀል ሚያዝያ 30 ቀን 2004 ዓ.ም ከቀኑ በዘጠኝ ሰዓት፣ በየካ ክፍለ ከተማ ቀበሌ 19 ሂልሳይድ ትምህርት ቤት አካባቢ የተፈጸመ ነው፡፡ ሟች ወይዘሮ ትዕግሥት መኮንን የትዳር አጋሯ ከነበረው ምናለ አቻም ከሚባለው ግለሰብ አንድ ልጅ የወለደች ሲሆን፣ ከሌላ የወለደቻቸው ሁለት ሕፃናት ልጆች አሏት፡፡

ከምናለ ጋር የነበራት ትዳር አልስማማ ስላላት የፍቺ ጥያቄ አቅርባ ነበር፡፡ የፍቺ ጥያቄውን ያልተቀበለው ምናለ አቻም ለበቀል በመነሳሳት በተጠቀሰው ዕለት በቤቷ መግቢያ ላይ ጠብቆ፣ እንደደረሰች ጭንቅላቷንና እግሮቿን ደጋግሞ በዱላ በመምታት እንድትወድቅ ያደርጋታል፡፡ በዚህ ጊዜ በተባባሪነት ተከሶ ጥፋተኛ የተባለው ዘለዓለም ውበት ወይም በቅፅል ስሙ ‹‹ጉቼ ውበት›› በሚባል መጠሪያ የሚታወቀው ግለሰብ ቤት ያስቀመጠውን አንድ ሊትር ሰልፈሪክ አሲድ፣ ሌላው ጥፋተኛ የተባለው ተባባሪ ነበረ ጎሹ ወይም በቅፅል ስሙ ‹‹ቀበሮው›› በሚል የሚጠራው ግለሰብ አምጥቶና ከፍቶ ሲሰጠው፣ ምናለ በመላ ሰውነቷ ላይ አርከፍክፎባት ተሰውረዋል፡፡

በአካባቢው የነበሩ ሰዎች ውኃና ወተት በማፍሰስ ጊዜያዊ ስቃይዋን ለመታደግ ቢሞክሩም ባለመቻሉ ወደ ሆስፒታል ተወስዳለች፡፡ ከሁለት ቀናት ስቃይ በኋላም ግንቦት 2 ቀን 2003 ዓ.ም ከሌሊቱ ዘጠኝ ሰዓት ሕይወቷ ማለፉን የዓቃቤ ሕግ የክስ ቻርጅ ይገልጻል፡፡ ዓቃቤ ሕግ በመሠረተው ክስ ላይ ያቀረበውን የሰውና የሰነድ ማስረጃዎች ማስተባበል ያልቻሉት ሦስቱም ግለሰቦች ጥፋተኛ ተብለዋል፡፡

No comments:

Post a Comment