Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Wednesday, April 25, 2012

ከሑመራ ከ140 በላይ ነዋሪዎች ታፍነው ወደ ኤርትራ ተወሰዱ

Source: ሪፓርተር ጋዜጣ
በትግራይ ክልል በቃፍታ ሑመራ ወረዳ በኤርትራ አዋሳኝ በሆነው የተከዜ ወንዝ ልዩ ስሙ ፅርግያ ግርማይ በተባለው አካባቢ፣ በባህላዊ መንገድ ወርቅ በማውጣት ላይ ተሰማርተው ከነበሩት መካከል ቁጥራቸው ከ140 በላይ ነዋሪዎች ማንነታቸው ባልታወቁ የታጠቁ ኃይሎች ታፍነው ወደ ኤርትራ መወሰዳቸውን በአካባቢው የሚገኙ የሪፖርተር ምንጮች ጠቆሙ፡፡ 

 በቃፍታ ሑመራ ወረዳ ደድሪስ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ በ1995 ዓ.ም. የተቋቋመው ‹‹ሀገረ ሰላም›› አዲስ የሰፈራ መንደር ነዋሪ ከሆኑት መካከል ቁጥራቸው እስከ 300 የሚደርሱ ነዋሪዎች፣ የኤርትራ አዋሳኝ በሆነው በተከዜ ወንዝ በባህላዊ መንገድ ወርቅ በማውጣት ሥራ ላይ ተሰማርተው ይገኛሉ፡፡

ባለፈው ቅዳሜ ሌሊት ማንነታቸው ያልታወቁ ከኤርትራ የመጡ የታጠቁ ኃይሎች ወንዙን ተሻግረው ከሌሊቱ አምስት ሰዓት አካባቢ በአንድ ላይ ተኝተው የነበሩትን ከ100 በላይ ነዋሪዎች ከበዋቸው ካደሩ በኋላ፣ ጠዋት አፍነው እንደወሰዱዋቸው የአካባቢው ምንጮች ለሪፖርተር አስረድተዋል፡፡

እንደ ምንጮቹ ገላጻ ከሆነ፣ አፋኞቹ ቀን ሲሰልሉ ውለው ድርጊቱን በሌሊት የፈጸሙ ሲሆን፣ በቁጥጥር ሥር ውለው ከታፈኑት መካከል አንዳንዶቹ ወንዙን በመሻገር ላይ ሳሉ ዋኝተው ማምለጥ ችለዋል፤ በአፋኞች ተተኩሶባቸው ጉዳት ሳያደርስባቸው ቀርተዋል፡፡ ይኼው ድርጊት ቅዳሜ ለእሑድ አጥቢያ የተደገመ ሲሆን፣ ሰባት ሰዓት ላይ ተጨማሪ ቁጥራቸው 40 የሚሆኑ ነዋሪዎች በተመሳሳይ ታፍነው ተወስደዋል፡፡

ምንጮች እንደሚሉት፣ ድርጊቱን ፈጻሚዎች በኤርትራ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ታጣቂዎች ሳይኖሩበት አይቀርም፡፡

ሦስት ሴቶችና አንድ አዛውንት ከታፈኑት መካከል ተለቀው የተመለሱ መሆናቸውም ከምንጮች ለማወቅ ተችሏል፡፡ ከታፈኑት መካከል ገ/መድህን ተኽላይ፣ እምባየ ፀሐየ እና ካሕሱ የተባሉት ግለሰቦች ካመለጡት መካከል ይገኙባቸዋል፡፡

የትግራይ ክልል ማስታወቂያ ቢሮ፣ የፀጥታ ኮሚሽንና የቃፍታ ሑመራ ወረዳ አስተዳደር ጉዳዩን አስመልክተን ለማነጋገር ብንሞክርም ማብራርያ ለመስጠት ፈቃደኞች አልሆኑም፡፡

የቃፍታ ሑመራ ወረዳ ፀጥታ ቢሮ ስማቸው እንዳይገለጽ የፈለጉ አንድ ኃላፊ ግን፣ ታፍነው የተወሰዱት ነዋሪዎች ከተለያዩ ወረዳዎች የመጡ መሆናቸውን አምነው ቁጥራቸውም ከ75 እንደማይበልጥ ገልጸዋል፡፡ የታፈኑትን ሰዎች ቁጥር ከሌሎች ኃላፊዎች በማጣራት ላይ ሳሉ፣ ሌላ ግለሰብ ስልኩን ተቀብለው፣ ‹‹ማን ነህ አንተ? ምን ፈልገህ ነው?›› በማለት ጥያቄ አቀረቡ፡፡ ማንነታችንን ስንነግራቸው፣ ‹‹ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ መጠየቅ ትችላለህ፤ ወደ ትክክለኛ ቦታ አልደወልክም፤›› በማለት ምላሽ ሰጥተው ሳይጨርሱ፣ ቢሮአቸው የሚመለከተው ጉዳይ መሆኑን ለማስረዳት ቢሞከርም፣ ስልኩን ጆሮአችን ላይ ዘግተው፣ በተደጋጋሚ ሲደወል ስልኩን ለማንሳት ፈቃደኛ አልሆኑም፡፡

የአፈና ድርጊቱ በአዲሱ የሰፈራ መንደርና በአጠቃላይ በወረዳው ውስጥ መደናገጥ የፈጠረ ሲሆን፣ ድርጊቱ ለሁለተኛ ጊዜ እሑድ ሌሊት ከተፈጸመ በኋላ የኢትዮጵያ የፀጥታ ኃይሎች ወደ አካባቢው ተንቀሳቅሰው ሁኔታውን ማረጋጋታቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ታፍነው ስለተወሰዱት ዜጎች ሁኔታ ግን በተመለከተ ምንም ፍንጭ አልተገኘም፡፡

No comments:

Post a Comment