Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Tuesday, June 5, 2012

በቤንች ማጂ ዞን በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተገደሉ

                   - ግጭቱ አሁንም አልበረደም
 By Finote Netsanet news no. second year, no.45
በቤንች ማጂ ዞን ሜኒኑ፣ ጉልዲያ፣ ሜኒትሻሻ፣ ቤሮ፣ እሹርማ እና በኮይ ወረዳዎች ለወራት የቀጠለው ግጭት ዳግም ማገርሸቱን የአካባቢው ምንጮች ጠቆሙ፡፡ 

በተለይ የፌደራል ፖሊስና የመከላከያ ሰራዊት በጥምረት በሚቆጣጠሯቸው ኮይ እና ቤሮ ሻሻ አካባቢዎች ከፍተኛ የፀጥታ ችግር እንዳለ የሚናገሩት ምንጮቻችን ግጭቱ ያገረሸው ግንቦት 12 ቀን 2004 ዓ.ም በአካባቢው ቢራ እና ለስላሳ የሚያከፋፍሉ አቶ አብርሃም የተባሉ ግለሰብ በአካባቢው በሚንቀሳቀሱት ታጣቃዎች መገደላቸውን ተከትሎ እንደሆነ ዘግበዋል፡፡

ፍኖተ ነፃነት ያነጋገረቻቸው አንድ የዞኑ ባለስልጣን በአካባቢው አሳሳቢ የሆነ የፀጥታ ችግር እንዳለ አምነው፣ ችግሩ ከአራት ወራት በላይ እንዳስቆጠረ ተናግረዋል፡፡ እኚሁ የዞኑ ባለስልጣን ጨምረው እንደ ገደለፁት ካለፉት አራት ወራት ወዲህ መኪናዎች ወደ ተለያዩ የወረዳ አካባቢዎች ሲንቀሳቀሱ በመንግስት ታጣቂዎች እንደሚታጀቡ አብራርተዋል፡፡ ባለሥልጣኑ እንደሚሉት የዞኑ የፀጥታ ችግር ከቁጥጥር ውጪ በመውጣቱ በአካባቢው የሚገኙት የፌደራል ፖሊስና የመከላከያ ሠራዊት አካላት እርምጃ በመውሰድ ላይ ይገኛሉ፡፡

የፍኖተ ነፃነት ምንጮች ባደረጉት ማጣራት እንደሞከሩት የፌደራል ፖሊስና የመከላከያ ሰራዊት ከመጠን ያለፈ ኃይል ተጠቅመው አካባቢውን ለማረጋጋት ሞክረዋል፡፡ ምንጮቻችን በዚህ የኃይል እርምጃ በመቶዎች የሚቆጠሩ የአካባቢው ነዋሪዎች እንደተገደሉ አስረድተዋል፡፡ ግጭቱ ከተባባሰባቸው አካባቢዎች ሸሽተው የወጡ ነዋሪዎች ለምንጮቻችን እንደገለፁት በየቀኑ ከአስር እስከ አስራ አምስት ሰዎች በግጭቱ ይገደላሉ፡፡ በአካባቢው የሚወጣውን የወርቅ መአድን ለመቆጣጠር የሚፈልጉ ከ15 በላይ የሚሆኑ ታጣቂ ሀይሎች በዞኑ ውስጥ እንደሚንቀሳቀሱ ከአካባቢው ያሰባስብናቸው መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ 

በተያያዘ ዜና በአካባቢው ያገረሸውን ግጭት ተከትሎ ከሚዛን ከተማ ወጪ ባሉት የዞኑ አካባቢዎች የስልክ ግንኙነት መቋረጡ ታውቋል፡፡ ከግንቦት 18 ጀምሮ የተቋረጠው የስልክ ግንኙነት በአካባቢው ያለውን ግጭት አደገኛነት የሚጠቁም መሆኑን የአካባቢው ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ ፍኖተ ነፃነት ስለ ግጭቱ መንግስት የሚያቀው መረጃ እንዳለ የተጠየቁት የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ሽመልስ ከማል የደረሳቸው መረጃ እንደሌለ ተናግረዋል፡፡ ፍኖተ ነፃነት የክልሉ ቃል አቀባይ የሆኑትን አቶ ሀሰንን ለማግኘት ያደረገችው ጥረት ስልካቸው ባለመስራቱ ምክንያት አልተሳካም፡፡

No comments:

Post a Comment