Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Monday, June 4, 2012

አማራ ተወላጆች እንዲፈናቀሉ ያዘዙትና በሙስና የተወነጀሉት ሽፈራው ሽጉጤ ካናዳ ይመጣሉ (አኢጋን)

Source: ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ (አኢጋን)
ተቃውሞ ፍራቻ ጉዞው በምስጢር አንዲያዝ መመሪያ ተላልፏል, በጉራፋርዳ የሚኖሩ የአማራ ተወላጆች እንዲፈናቀሉ ትዕዛዝ የሰጡትና በከፍተኛ የሙስና ወንጀል ተጠያቂ እንዲሆኑ በፓርቲያቸው የተበየነባቸው የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽፈራው ሽጉጤ የሚመሩት ቡድን ካናዳ ለስራ ጉብኝት እንደሚመጣ ተሰማ። 

የአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ (አኢጋን) ምንጮች እንዳስታወቁት አቶ ሽፈራውን ተቃውሞ እንዳይገጥማቸው ጉብኝቱ በተለይ በውጪ የሚገኙት የተቃዋሚ ፓርቲ ደጋፊዎች እንዳይሰሙት በምስጢር እንዲያዝ መመሪያ ተሰጥቶ ነበር።

አቶ ሽፈራው ካላቸው የፖለቲካ ሥልጣን በተጨማሪ የሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ የቦርድ ሰብሳቢ ሲሆኑ የዩኒቨርሲቲውን ፕሬዚዳንት፣ የእርሻ ኮሌጁን ዲንና የተለያዩ ሹመኞችን አስከትለው በካናዳ በሚገኘው የሳስካችዋን ዩኒቨርሲቲ ጉብኝት ለማድረግ ሰኔ 3ቀን 2004ዓም (ጁን 10 ቀን 2012) ካናዳ ይደርሳሉ፡፡ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ከወራት በፊት በጉራፋርዳ ይኖሩ በነበሩ የአማራ ተወላጆች ላይ ለተፈፀመው ግፍ መሪ ተዋናይ መሆናቸውን በስማቸው ተጽፎ የፈረሙበትን ደብዳቤ ዋቢ በማድረግ የጋራ ንቅናቄያችንን ጨምሮ በርካታ የአገርና የውጪ መገናኛዎች እንደመሰከሩባቸው ይታወሳል።

በተለይም የድርጊቱ ሰለባ የሆኑት እምባቸውን እያፈሰሱ የደረሰባቸውን በደል ሲገልፁ ያደመጡ ሁሉ በወቅቱ ድርጊቱን ከመቃወም ባለፈ “አማራው መደራጀት አለበት” እስከማለት አቋም እንዲይዙ የተገደዱበት ሁኔታ ተፈጥሮ ነበር። አቶ ሽፈራው “አንድም የተፈናቀለ ሰው የለም” በማለት ድርጊቱን ቢክዱም ከጉራ ፈርዳ የተፈናቀሉ ወገኖቻችን ሲቃ እየተናነቃቸው አገር አልባ መደረጋቸውን፣ በደላቸውን የሚሰማ አካል እንዳጡና ሃብትና ንብረታቸው ተዘርፎ፣ ቤታቸው ተቃጥሎ እንደ ለማኝ ፌስታል አንጠልጥለው እንዲባረሩ የተደረጉበትን ሁኔታ የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት(መኢአድ) እና የሪፖርተር ጋዜጣ በስፋት ዘግበውታል፡፡ 

በተለይ መጋቢት 23ቀን 2004ዓም በታተመው የሪፖርተር ጋዜጣ ተፈናቃዮቹ ሁኔታውን በሚከተለው መልኩ ገልጸው ነበር፡- “…ነፍሰ ጡር እናት ሌሊት ወልዳ ሲነጋ የሰዓታት ዕድሜ ካለው ልጇ ጋር ከነፍራሿ ደጅ ተጥላለች፤ ነፍሰ ጡሮች ተሰደዋል፤ የስምንት ወር ዕድሜ ካላቸው ጨቅላ ሕፃናት ጀምሮ በርካታ ሕፃናት ከሚያጠቡ እናቶቻቸው ጋር አብረው ታስረዋል፤ የሚላስ የሚቀመስ አጥተው በረሃብ ተጠብሰዋል፤ በነፍስ ወከፍ እስከ 3ሺህ እግር ቡና ዛፍ፣ አቡካዶ፣ ማንጐ፣ ፓፓያና ሙዝ የተከለ እንዲሁም በርካታ የንብ ቀፎ የሰቀለው፣ በከብትና በዶሮ እርባታ ላይ የተሰማራው ገበሬ ያመረተውንና ያፈራውን ሀብትና ንብረት ጥሎ ጨርቁን በፌስታል አንጠልጥሎ እንዲወጣ ተደርጓል፡፡

 ‘ምንም ይዛችሁ ስላልመጣችሁ ምንም ይዛችሁ አትሄዱም’ እየተባሉ ንብረታቸውን ሜዳ በትነው እንዲሄዱ ተደርገዋል፤ በታጣቂዎችና በፖሊስ ሃይል ተደብድበዋል…” “የሰሚ ያለህ” በማለት አቶ መለስ ዘንድ በመቅረብ ይኖሩበት ወደነበረው ጉራፋርዳ ወረዳ እንዲመለሱ ወይም ደግሞ ወደ አማራ ክልል ተመልሰው ተለዋጭ ቦታ ተሰጥቷቸው በግብርና ሥራ የሚሰማሩበት ሁኔታ ይመቻችላቸው ዘንድ አቤቱታ ለማቅረብ ወደ አዲስ አበባ ከመጡት 600 ገደማ ከሚደርሱት ተፈናቃዮች መካከል አብዛኛዎቹ በፖሊሶች በኃይል እየተገፈተሩ በአራት የሕዝብ ማመላለሻና በአንድ ታክሲ ተጭነው ወደ ደብረ ብርሃን ተወስደዋል፡፡

ለዚህ ሁሉ ግፍና በደል ተጠያቂ የሆኑት አቶ ሽፈራው ሽጉጤ በሌላም በኩል ከየካቲት 5 አስከ የካቲት 11 ቀን 2004 በክልሉ ፓርቲ አማካይነት በተካሄደ የከፍተኛ አመራሮች ግምገማ በከፍተኛ የሙስና ወንጀል እንዲጠየቁ የተበየነባቸው የህወሓት/ኢህአዴግ ሹመኛ ናቸው። የጋራ ንቅናቄያችን በክልሉ ያሉትን ምንጮች በመጥቀስ በወቅቱ እንደዘገበው በአቶ መለስና በተከታዮቻቸው ቋንቋ “ኪራይ ሰብሳቢና ሙሰኛ” የተባሉት አቶ ሽፈራው ለቀረበባቸው ክስ ሲመልሱ “እኔ ብቻዬን አይደለሁም። ከጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ባለቤት ወ/ሮ አዜብ መስፍን ጋር በጋራ ገንዘብ ወስደናል። የምንጠየቅ ከሆነ ሁለታችንም ህግ ፊት መቅረብ አለብን። ብሩን መመለስ ካለብንም ሁለታችንም መመለስ አለብን” ማለታቸው ይታወሳል።

አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ከግምገማው በኋላ አስር ይገጥማቸዋል፤ በዋናው የኢህአዴግ ግምገማ ላይ ይገመገማሉ፤ የሚል እምነት የነበራቸው የክልሉ ሹመኞች የግምገማው ውጤት በመገልበጡ ማዘናቸውን ተናግረው ነበር። ከማዘናቸውም በላይ ወደፊት እንዴት አብሮ መስራት እንደሚቻል ያሳሰባቸው ሹመኞች “አቶ ሽፈራው በከፍተኛ ሁኔታ የቡና ንግድ በተሰማራ ድርጅት ውስጥ የላቀ የአክሲዮን ባለ ድርሻ መሆናቸው እየታወቀ ዝም የተባሉት ወ/ሮ አዜብን ተንተርሰው ነው፤ ተነካክተዋል። ይህ ደግሞ አገራዊ በሽታ ነው” ሲሉ አቶ መለስ ታጋይዋን ሚስታቸውን ለመሸፈን ሲሉ የግምገማውን ውጤት መገልበጣቸው ቅሬታ መፍጠሩን አመልክተው ነበር።

በካናዳ ሳስካችዋን ዩኒቨርሲቲ ለስራ ጉብኝት የሚመጡት አቶ ሽፈራው ተግባራቸውን ስለሚያውቁት ጉብኝታቸውን ከተቃውሞ ለመከላከል ሲሉ ምስጢራዊ እንዳደረጉት የገለፁት የጋራ ንቅናቄያችን የደቡብ ምንጮች ምናልባትም የጉብኝታቸው ጉዳይ ይፋ መሆኑን ተከትሎ አቋማቸውን ሊቀይሩ እንደሚችሉም ገምተዋል። አክለውም ሰሞኑን በታላቅ የዓለማችን መድረክ ላይ አቶ መለስ የገጠማቸው አስደንጋጭና ያልተደበቀ መብረቃዊ ተቃውሞ ከፍተኛ የመገናኛ ሽፋን በማግኘቱ የተነሳ አቶ ሽፈራውም ከተመሳሳይ ውግዘት ለመዳን ጉብኝታቸውን በዩኒቨርሲቲው ኃላፊዎች ብቻ እንዲከናወን ሊደርጉት እንደሚችሉም ጠቁመዋል።

የጋራ ንቅናቄያችን ዋና ዳይሬክተር አቶ ኦባንግ ሜቶ በከተማዋ ለረጅም ዓመታት የኖሩ ሲሆን ትምህርታቸውን የተከታተሉበትና በተለያየ የተማሪ እንቅስቃሴዎች ውስጥ ተሳታፊ የነበሩበት የሳስካችዋን ዩኒቨርሲቲ፣ በቅርቡ 100ኛ ክብረ በዓሉን ሲያከብር “ተጽዕኖ ፈጣሪ” በማለት ከመረጣቸው 100 የቀድሞው ተማሪዎቹ መካከል አቶ ኦባንግ እንደሚገኙበት ከዩኒቨርሲቲው መረጃ ለማወቅ ተችሏል።

አቶ ሽፈራው ህጻናት ሳይቀሩ ክልሉን ለቀው እንዲወጡ ቀነ ገደብ ወስነው ደብዳቤ ትምህርት ገበታቸው ድረስ የላኩ የህወሓት/ኢህአዴግ አገዛዝ ታዛዥ ቢሆኑም የሚያስተዳድሩት ሰፊ ኅብረተሰብ ድጋፉን እንዲያነሳ ቅስቀሳ እየተደረገባቸው ሲሆን፣ በሌላ በኩል እሳቸውን የሚተካው ሰው ህዝቡ እንዲቀበለው የውስጥ ለውስጥ ስራ እየተሰራ መሆኑን በክልሉ የጋራ ንቅናቄያችን ምንጮች አመልክተዋል።

No comments:

Post a Comment