Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Monday, September 3, 2012

አቶ መለስ ዜናዊ ለትውልድና ለሀገራችን ጥለውት ያልፉት እኩይ፣ መራራና አሳዛኝ ሀቆች(ከፊሊጶስ)

የአቶ መለስ፣ የኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊያን ግንኙነት ሁሌም ይደንቀኛል። በሀገርና በትውልድ ላይ የፈጸሙትንና ጥለውት የሄዱትን ከትውልድ ወደ ትውልድ ይሚትላልፍ መርዝ ሳስብ፤ ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያዊያን የነበራቸውን ጥላቻ ስቃኝ ፤በ’ርግጥ የሰው አዕምሮ ተመራምሮ ይደርስብት ይሆን? እላለሁ። አሁንም ከኢትዮጵያና ከዚች ዓለም ተለይተው ሄደው ግፋቸውን ሳስታውስ እጅግ አድርጎ ይገርመኛል ። ዘፋኙ ምን ነበር ያለው?……’’….ግርም ያደርገኛል ያሰበኩት እንደሆን ሰው በገዛ ሀገሩ ስደተኛ ሲሆን።….”እስቲ ባለፉት አመታት አቶ መለስ በኢትዮጵያና በኢትዮጵያዊያን ላይ የሰሩትንና የፈጸሙትን መራራ ሀቆችና ለዚህ ትውልድ ጥለውት ያለፉትን ታሪክ እጅግ ባጭር ባጭሩ (የውቅያኖስን ውሀ በጭልፋ ጨለፎ ለመጨረስ እንደመሞከር ይቆጠራል።) እናስታውስ።

1ኛ/ አቶ መለስ፣ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነታቸው፤ አቶ መለስ ዜናዊ በኢትዮጵም ሆነ በኢትዮጵያዊነታቸው አያምኑም ነበር። ”ኢትዮጵያዊ ነኝ” ወይም ”ኢትዮጵያ ሀገራችን” ወይም ”ሀገሬ” ሲሉ ተሰምተው አያውቁም።

አቶ መለስ የድሮው ለገሰ ዜናዊ ሚያዚያ 30/1947 በኢትዮጵያ በትግራይ ክፍለ ሀገር በአደዋ ተወለዱ። ገና ከጅምሩ አቶ መለስ ለኢትዮጵያና የኢትዮጵያዊያን አልታገሉም። የወላጆቻቸው ክፍለ ሀገር፤ “ኤርትሪያና ትግራይ የኢትዮጵያ ቅኝ ግዛቶች ናቸውና።” እሳቸውም በኢትዮጵያዊነታቸው አያምኑም ነበር። ሕወሓትን እንደተቀላቀሉ፤ ላልተወሰነ ግዜ ጠፍተው ወደ ኤርትራ፣ ወደ እናታቸው መንደር አዲቋላ ነበሩ። ከዚያም ተመልስው ለሕወሓትን እጅ ሰጡ። የሻአቢያን ትግል ለመቀላቀል ፈልገው ግን ስላልተመቻቸላችው ወይስ ተቀባይነት ስላጡ? ይህ መጠናት ያለበት ጉዳይ ነው። 

ትውልድ እውነቱን እንዲያውቅ። (‘’ኤርትራ ከየት ወዴት” የሚለውን የራሳቸውን ድርሳን ይመልከቱ) ታዲያ ”ኢትዮጵያዊ ያልሆኑና በኢትዮጵያ ቅኝ ተገዥ የሆኑት” አቶ መለስ ኢትዮጵያን ለ21 ዓመት የቻሉትን ያህል ከፋፍለውና አፈራርሰው ገዙ። ሸጡ። በታሪካችንና በትውልድ ላይ ቀለዱ።

2ኛ/ አቶ መለስ ስለ ኢትዮጵያ ታሪክ ያላቸው ግንዛቤ፤አቶ መለስ ኢትዮጵያ የመቶ ዓመት ታሪክ ያላትና በአጼ ምኒሊክ የተቆረቆረች ሀገር ናት ብለው የራሳቸውን የፈጠራ ታሪክ ያምናሉ። ማመን ብቻ አይደለም፤ እምነታቸውን ባገኙት መድረክና አጋጣሚ ሁሉ ሌላውን ወገን፣ በተለይም ለአፍሪካዊያንና ለምዕራባዊያን በኢትዮጵያዊያን ላይ የበታችነትና የንቀት ስሜት እንዲያሳድሩ ከማስረዳትና ታሪክን ከማዛባት ቦዘነው አያውቁም። ደጋፊዎቻቸውንም በዙ ድርሳናት እንዲደርሱ አድገዋል። የክህደትና የፈጠራ ታሪካቸውን ለፓለቲካ ግባቸው ተጠቀሙበት። ከቅርብ ግዜ ወዲህ ግን ”ኢትዮጵያ ረጅም ታሪክ ያላትና ታላቅ ሀገር ነች።” ለማለት ሲከጅሉ ተሰምተዋል። ዋይ!…..ንሰሀ ሊገቡ አስበው ነበር ይሆን? ወይስ አዲሱ የፓለቲካ አክሮባት? ግን ተቀደሙ።

3ኛ/ አቶ መለስና የኢትዮጵያ ባንዲራ፤ አቶ መለስ ለኢትዮጰያ ባንዲራ ያላቸው ጥላቻ እጅግ የከፋ ብቻ ሳይሆን “ከጨርቅ ጉዳይ የለንም!” በማለት የራሳቸውን ባንዲራ ሰርተው፤ የኢትዮጵያን ህዝብ ሳይፈልግ ”እንዲቀበል” አድርገውታል።

4ኛ/ አቶ መለስና የኢትዮጵያ ሠራዊት፤አቶ መለስ ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያዊያን ያላቸውን ጥላቻና ማን አለበኝነት ካሳዮበት መንገድ አንዱ በብዙ ድካምና ወጭ ሲገነባ የኖረውን የኢትዮጵያን ሠራዊት በአንድ ጀምበር በመበታተንና በማፈራረስ የጎዳና ተዳዳሪ አደረጉት። የባህርና የጦር መርከቦቻቸን ከፊሎቹን ለሻአቢያ ሰጡ፤ ሻአቢያ የማትፈልጋቸውን ደግሞ ለታሪካዊ ጥላቶቻችን ተሸጡ።

5ኛ/ አቶ መለስ፣ የኢትዮጵያ ለዕልናና ዳር ድንበር፤በ1983 አቶ መለስ ከደርግ ጋር በሚደራደሩበት ወቅት፤ የሳቸው አሸናፊነተ ሲረጋገጥ፤ አሜሪካዊ አደራዳሪ ኸርማን ኮኸን ለንደን ላይ ‘’የባህር በር ጉዳይ እንዴት ነው? መቼም ቢሆን ኢትዮጵያ የባህር በር ያስፈልጋታል።’’ ሲሏቸው፤ የአቶ መለስ መልስ “ስለ ባህር በር ጉዳይ ከሻአቢያ ጋር እንነጋገርበታለን” ነበር ያሉት። እናም ታሪካዊ ጥላቶቻችን ዘመናት ሙሉ ኢትዮጵያ የባህር በር የሌላት የማድረግ ህልም አቶ መለስ እውን አደረጉላቸው። በእርግጥ አቶ መለስ ሌላም ዓላማ ነበራቸው። ኢትዮጵያን ከቻሉ አፈራርሰው፣ ካልቻሉ ደግሞ ደካማና የተከፋፈለ ህዝብ በመፍጠር፣ ታላቋን ትግራይን በመመስረት ከኤርትራ ጋር በመስማማት አሰብን የትግራይ ማድረግ ነበር። ይህን ህልማቸውን እውን ሳያደርጉ አቶ መለስ አለፉ። ግብረ-አበሮቻቸው ግን ”ትግላችን ይቀጥላል” በማልት ሲፎክሩ ይሰማሉ።

6ኛ/ አቶ መለስና የኤርትራ ተውኔት፤ተውኔት-1፡ አቶ መለስ “ኤርትራ የኢትዮጵያ ቅኝ ግዛት ነች።” በማለት፤ ይህን ቋንቋ ሊገጸው፣አዕምሮ ሊያስበው የሚከብደውን ዓይን አውጣ የክፍለ ዘመኑን የክህድት ታሪክ ለመስበክና ለማስተማር ያላቸውን ሀይል ሁሉ ተጠቀሙ።

በታሪክና በትውልድ ላይ አፌዙ። ተውኔት-2፡ ”ኢትዮጵያዊያን ስለ ኤርትራ ምንም የሚመለከታቸው ነገር የለም።” በማለት መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ የዳር ተመልካች ሆኖ ቀረ። ለሺ’ ዘመናት ሙሉ ሲከፈል የነበረው የደምና የአጥንት መሰዋዕትነት ትርጉም የሌለውና ”የትምህክተኞች” እንደነበር በመግለጽ፤ በጀግኖች ሙታን ወገኖቻችን ላይ ሲደነፉ ኖሩ።

ተውኔት-3፡ ‘’ነጻነት ወይም ባርነት’’ ለሚጠይቀው ህዝበ ውሳኔ ህጋዊ እውቅና በመስጠት ኢትዮጵያን የመበታተኑን የጥላቶቻችንን ሴራ ተገበሩ:: አቶ መለስ በዚህም አድራጎታቸው በጣም ይመኩ ነበር።

ተውኔት-4: “ኤርትራ የኢትዮጵያ ቅኝ ግዛት ነበረች።” በማለት “ከኢትዮጵያ ቅኝ ግዛት ነጻ መውጣቷን” ለተባበሩት መንግሥታትና ለአፍሪካ አድነት ድርጅት ደበዳቤ በመጻፍ እውቅና እንዲሰጧት ተማጸኑ፤ አቶ መለስ። ባለስልጣናቱ ከዓለም ህግ አንጻር እንደማይቻል ሊያስረዷቸው ቢሞክሩ (ከቡትረስ ቡትረስ ጋሊ ውጭ፤ እሳቸው ያገራቸውን የግብጽን ዓላማ ማስፍጸም ነበረባቸው።) ”ባገራችን የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ አትግቡ” አሏቸው።

ተውኔት-5: በኤርትራ ምድር ከአሁን በኋላ ጥይት አይጮህም። ወ.ዘ.ተ.
አቶ መለስ ኤርትራ ከኢትዮጵያዊ እንድትገነጠል ሳይሆን ገንጥለዋል። አቶ ኢሳያስ አፈወርቂም የአቶ መለስን ያሀል የደከሙ አይመስለኝም። አቶ መለስ ኤርትራን ገንጥለውና አስገንጥለው ከጨረሱና ሁሉንም ካመቻቹ በኋላ፤ የኤርትራ ተወላጅ ወገኖቻችን ኢትዮጵያን እንዲገዙ ይፈልጉ ነበር። (በእርግጥ ፍታዊ በሆነ መንገድ ከሆነ አቶ ኢሳያስም የኢትዮጵያ መሪ ቢሆኑ የኢትዮጵያ ህዝብ ደስተኛ በሆነ። ችግራችን ከሚከተሉት ዓላማ እንጅ።) ለዚህም ሲሉ በሻአቢያ የወርቅ ጥርሳቸውን ሳይቀር እየተወለቀ ለተባረሩት ዜጎች፤ ”ይህም ሲያንስ ነው፣ እንዲያውም ኢትዮጵያ ካሳ መክፈል ነበረባት” ነበር ያሉት። እናም ቀጠሉ… ለሻቢያዎች ኢትዮጵያዊያኖችን የሚያስሩብት ከርቸሌ አዘጋጅተው አሳሰሩ፣ አስገርፉ፣ አስገደሉ። ሻአቢያዎች የሀሰት ገንዘብ አሳትመው የፈለጉትን ነገር ሁሉ እንዲሸጡ፣ እንዲገዙ፣ እንዲለውጡና እንዲያግዙ ተደረገ። እናም ሻአቢያዎች ከአፍሪካ አንደኛ ቡና ላኪ ሆኑ።

7ኛ/ መሬት ለሱዳንና ኢትዮጵያን መግዛት ለሚፈለጉ ሁሉ፤አቶ መለስ ኤርትራን ገንጥለውና አስገንጥለው ከወገኖቻችን ለያይተውን ብቻ አልቀሩም። ስልጣናቸው መደላደሉን ሲያረጋግጡ፣ ሱዳኖች ጫካ በነበሩበት ወቅት ለዋሉላቸው ውለታና ተቀናቃኝ ጠላት ቢነሳባቸው አሳልፈው እንዲሰጧቸው የኢትዮጵያዊያን ገበሬዎችን በማባረር የኢትዮጵያን ክቡር መሬት ቆርሰው በገጸ-በረከትነት አበረከቱ። አቶ መለስ በዚህ አላቆሙም….. የሀገሪቱን አንጡራ መሬትና ማዕድን ዜጋውን እያፈናቅሉ ለባዕዳንና ለታሪካዊ ጠላቶቻችን ቸበቸቡ። እስከልተ ሞታቸው ድረስ እንግሊዝን የሚያክል ሀገር እንደሸጡ ይገምታል። አላማውም ኢትዮጵያ ማፈራረስ ቀላሉ መንግድ በመሆኑ ነው።

8ኛ/ የአቶ መለስና ኢትዮጵያዊያን ምሁራን፤አቶ መለስ የስልጣን ኮርቻቸውን እንደተፈናጠጡ፣ አ’ዱና ዋና ስራ አድርገው የያዙት ኢትዮጵያዊ ስብእናና ለኢትዮጵያ ክብርና አንድንት ሊታገሉ ይችላሉ ያሏቸውን ምሁራንን ከየትምህርት ትቋሞት አሳደዋል። አባረዋል። ገለዋል። የትምህርት ተቋማቱንም ለሆዳቸው ባደሩ ሆድ አምላኪ ‘’ምሁራንን’’ ተኩበት። ዓላማቸውም ተጠራጣሪ፣ የማይትማምን፣ ለኢትዮጵያ አንድንትና ለክብሩ ብዙም የማይጨነቅ፣ እንደገዥዎቻችን በአፍቅሮ ንዋይ የታወረ፣ ገንዝብ (ሀብት) የሁሉም  ነገር መጀመሪያና መጨረሻ ነው ብሎ የሚያምን ለውጭ አለም ማንነቱን ያስረከበ ትውልድ ለማፍራት የታቀደ ነበር።ነውም።

9ኛ/ የአቶ መለስ የዘር ጥላቻ፤አቶ መለስ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን ያፈራረሳል ብለው የተጠቀሙበትና ዋና መሳሪያ ያደረጉት ኢትዮጵያዊያንን በተቻለ መጠን በዘርና በቋንቋ በመከፋፈል፤ ከትውልድ ትውልድ የሚተላልፍ ጥላቻንና ቂምን በማሰራጨት፤”የክልል ይገባኛል” የርስ-በ’ርስ እልቂት እንዲኖር ማድረግ ነው። ” ከወርቅ ዘር መወልዴ፣ ለወላይታው አክሱም ምኑ ነው፣ ወዘተ. የመሳሰሉትን አባባሎቻቸውን ስናሰብ፣ አቶ መለስ የጥላቻና የበታችነት ስሜታቸውን ለመወጣት፤የኢትዮጵያን የህዝብ እልቂት እንደማለዳ ጸሀይ ይናፍቁና ሌት ተቀን ይደክሙ ነበር።

10ኛ/ አቶ መለስና የኢትዮጵያ ሃይማኖት፤ አቶ መለስ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን አዳክሞ ያፈራርሳታል ብለው ካምኑበት ውስጥ አንዱ በሃይማኖት ከፋፍሎ እርስ በ’ርስ ማናቆርና ማበጣብጥ ነው። በተለይም የኦርቶዶክሳዊያንን ዶግማ እምነት በማፈራረስ፤ ጳጳሱን በማባረር ከራሳቸው መንደር የሚወልዱ “ጳጳስ” አስቀመጡ። ቤተክርስቲያንን ለሁለት ከፈሉ። እስልምናንም ከክርስቲያኑ ጋር ማበጣበጡ እንደፈለጉት አልሆን ሲል እርስ-በርስ ለማነካከስ ብዙ ጥረዋል። ሞት ቀደማቸው እንጅ።

11ኛ/ የአቶ መለስ ሰባአዊ ‘ረገጣዎች፤አቶ መለስ ገና ጫካ እያሉ ከ’ርሳቸው የተለየ ሀሳብ ያራምዳሉ ወይም ያስባሉ ብለው የጠርጠሯቸውን፤ በተለይ ደግሞ ኢትዮጵያዊነትን በሚያንጸባርቁና ትግላችን የመደብ ትግል ነው በሚሉ ታጋዮችን ያለ ‘ርኅራሄ ‘ረሽነዋል። አስረሽነዋል። መሀል ሀገር ከገቡም በኋላ በተለያዮ የሀገሪቱ ክፍሎች ዜጎች በቀለማቸው፣ በቋንቋቸውና በአመለካከታቸው ብቻ ከገደል ከነ ነፍሳቸው ተወርውረዋል። ቤታቸው ተዝግቶባቸው እንዲቃጠሉ ተደርጒል። ተረሽነዋል። ተሳደዋል። ሰላማዊ ሰልፍ የወጡ በጥይት ተደብድበዋል። ታስረው ተገርፈዋል። ዜጎች በገዛ ሀገራቸው ስደተኛና እንደሁለትኛ ዜጋ ተቆጥረዋል። አቶ መለስ ከወዳጃቸው ከአቶ ኢሳያስ አፈወርቂም ጋር በኢትዮጵያን ሀብትና ንብረት አዘራረፋ ላይ አለመስማማት ሲፈጠር “አማራ ለያይቶን እንጅ፤ እኛ እኮ በአንድ ሳንባ መተንፈስ የምንችል አንድ ህዝቦች ነን!” እንዳልተባለ ሁሉ፤በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎችን ማግደው አቃጠሉ። ብዙ ዜጎችንም ተወልደው ካደጉበትና በስጋም በነፍስም ከተሳሰሩበት ወገናቸው ለይተው አባረሩ። ለአሜሪካ ተላለኪ በመሆንም በሱማሊያ ጉዳይ ጣልቃ በመግባት ኢትዮጵያዊያን ወታደሮች ሬሳቸው በመቋድሾ ጎዳናወች እንዲጎተትና የዓለም መሳለቂያ በማድረግ ከትውልድ ትውልድ የሚተላልፍ ጥላቻና ቂም በቀል ዘሩልን።

12ኛ/አቶ መለስ፣ የሀገር ሀብትና ሙስና፤በአጠቃላይ ማለት ይቻላል፤ የሀገሪቱ ሀብት በሳቸው አካባቢ ባሉ ሰዎች፣ ለስልጣናቸው ታማኝና ለኢትዮጵያን ኢትዮጵያዊያን ደንታ በሌላቸው ባባእዳን የኢትዮጵያ ጠላቶች በሆኑ ዜጎች እጅ እንዲገባ አደረጉ። ሀገሪቱን የግል ሀብታቸውና ንብረታቸው በማድረግ የኢትዮጵያ ህዝብ ግን የበይ ተመልካች ሆነ። ከፊሉ ተሰደደ። ከፊሉንም በርሀ፣ ባህርና ውቅያኖስ በላው። ወጣት እህቶቻችን ለዝሙትና ለአረብ ግርድና አደሩ። አንዳንዶቹም እራሳቸውን አጠፋ። በፈላ ውህ ተቀቀሉ። ህጻናት ለስዶማዊያን ሳይቀር በጉዲፈቻ ተቸበቸቡ። ኢትዮጵያዊ ከዓለም ዜጋ ሁሉ የተጠላና የተዋረደ ሆነ። አቶ መለስ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያን ከምድረ-ገጽ መጥፋት ከሚፈልጉ ምእራባዊ አጋሮቻቸው ቢያንስ በአመት 4 ቢልዮን ዶላር ያገኙ ነበር። ግን ለሀገሪቱ ልማት የዋለው 14% ብቻ መሆኑን የተባበሩት መንግስታት አረጋግጦላቸዋል። ቀሪው ግን የአቶ መለስንና የመሰሎቻቸውን ካዝና እያጣበበ፣ኢትዮጵያኖችን ግን እያራቆተ ነው። ከ11.4 ቢሊዎን ዶላር በላይ በውጭ ሀገር ባንኮች አስቀምጠዋል። በቀርቡ ደግሞ ገዥዎቻችን በያዝነው ዓመት ብቻ ከ3 ቢሊዎን ዶላር በላይ ከሀገር አሽሽተዋል። እንገዲህ ይህ ጸሀይ የሞቀው ዓለም ያወቀው ነው። በድብቅ፣ በቤተሰብ ስምና በንግድ ስም 21 ዓምት ሙሉ የተዘረፈውን እሱ ይቁጠረው። ሙስናማ በአቶ መለስ ዘመን አዲሱ ባህላችን አድርገውልናል።

13ኛ/ አቶ መለስና ፍትህ፤ የአቶ መለስ ፍርድ ቤቶች አስቂኝና አሳዛኝ ቲያትር ቤቶች ናቸው። የፈለጉትን ሰው በፈለጉት መንገድ በአንድ ቀን ውስጥም ቢሆን ህግ አርቅቀው የማሰር፣ የመወንጀል፣ የመግደልና የመፍረድ መብት በእጃቸው መዳፍ ውስጥ ነው። በአሁኑ ወቅት ብዙ ዜጎች በእስር ቤት በፍትህ እጦት ይሰቃያሉ።

14ኛ አቶ መለስ፣ ተሳዳቢነትና ውሸታምነት፤አቶ መለስ የበታችነት ስሜታቸው ሲገነፍልባቸውና የተደፈሩ ሲመስላቸው፤ አንድ አዕምሮው የተነካ ሰው እንኳን ቢናገረው ሊቀፈን የሚችል የስድብና የንቅት ቃላቶችን በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ ከመለደፍ ቦዝነው አያውቁም ነበር። ውሸታምነታቸው ግን አገርን ሲያፈርስና ህዝብን ሲያበጣብጥ ከመኖሩ አልፎ፤ ተከታዮቻቸው ሞታቸውን እንኳን ሲዋሹን ከርመዋል።

ማጠቃለያ፤
አቶ መለስ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን የማፍረስና የማጥፋት ተግባራቸውን እስከመጨረሻ እስትንፋሳቸው ድረስ ሰርተው በጽናት አልፈዋል። ስለዚህም ተከታዮቻቸው ‘’ሳያርፍ ያረፈው መለስ” ቢሏቸውና ሌላም ሌላም የመወድስ ስም ቢያወጡላቸው ያንሳቸዋል እንጅ አይበዛባቸውም። በእርግጥ አላማ አድርገው የተነሱበትን ሙሉ በሙሉ አላሳኩም። ኢትዮጵያ የምትባል ሀገርና ዜጋ አሁንም አለና። እንዲያውም ይህ ትውልድ አቶ መለስና ባልደረቦቻቸው ለፈጸሙብን ግፍና በደል፤በኢትዮጵያዊነታችን ላይ ላደረሱብን ውርደትና ከፋፍልህ ግዛው የበለጠ ግንዛቤ እያገኘን መ’ተናል።

አዎ…አቶ መለስ ላይመለሱ ሄደዋል። ነገር ግን ላለፉት ዓመታት የደከሙበትና የለፉበት የጥላቻ፣ የዘረኝነት፣ የስደት፣የክህደትና የሙስና በአጠቃላይ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን የማፍረስና የማጥፋት ዓላማቸውን ለተከታዮቻቸው ጥለው አልፈዋል። አዲሱ ገዥዎቻችን ደግሞ የአቶ መለስን ዓላማ ተከትለው እስከመጨረሻው እንደሚጓዙ አበክረው ገልጸውልናል። ታዲያ እኛስ አሁንም እንዳለፈው በዚሁ በተገዥነት ጉዞ እንቀጥላለን? ወይስ ካለፈው ተምረን፣ አዲስ የትግል ስልት ቀይሰን ኢትዮጵያን ከመፈራረስ አድነን፣ ሁሉም ዜጎቿ በፍትህና በእኩልነት የሚኖሩባት የሁላችን ሀገር እገነባለን? ጥያቄውና ጠሪው ለሁላችንም ነው።
——————-//——————
ፊልጶስ / ጳጉሜ 3/2004 ኢ-ሜል፡philiposmw@gmail.com
(በዚህ አጋጣሚ ይህችን የመለስን ምግባር እንድጽፍ ሀሳቡን ላቀረብክልኝና ለገፈፋህኝ ለያደቴ ሙሉጌታ የከበረ ምስጋና
ይድረስህ።)http://www.zehabesha.com/?p=10059

No comments:

Post a Comment