Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Wednesday, April 11, 2012

ለመንገድ በተቆፈረ ጉድጓድ ውስጥ አንድ ሰው ገብቶ ሞተ

By Reporter 

“ግለሰቡ ሕይወቱ ያለፈው ምንም ምልክት ባለመኖሩ ነው”  የአካባቢው ነዋሪዎች "

የአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን ከጄኔራል ዊንጌት እስከ አስኮ ድረስ እያሠራው ባለው መንገድ ላይ በተቆፈሩ ጉድጓዶች ምክንያት፣ አንድ ግለሰብ ከትናንትና በስቲያ ከምሽቱ አራት ሰዓት አካባቢ ወደ ቤቱ ሲጓዝ ገብቶ ሕይወቱ ማለፉን የአካባቢው ነዋሪዎች ለሪፖርተር ገለጹ፡፡ በመንገዱ መሠራት ምክንያት በአካባቢው ኤሌክትሪክ ባለመኖሩና የሚያሠራው ወይም የሚሠራው አካል ምልክት ባለማድረጋቸው መሆኑንም ተናግረዋል፡፡

የእስራኤል ኩባንያ በሆነው ትድሀር ኤክስካቬሽን ኤንድ ኧርዝሙቪንግ ሊሚትድ በሚባለው ሥራ ተቋራጭና በዩኒኮን አማካሪ ድርጅት ተቆጣጣሪነት በመሠራት ላይ የሚገኘው መንገድ በአሁኑ ጊዜ እየተፋጠነ ቢሆንም፣ አንፀባራቂ ምልክቶችና ከልካይ ምልክቶች  በሥራ ተቋራጩ፣ በአማካሪው ወይም በባለሥልጣኑ ባለመደረጋቸው የተለያየ መጠን ያላቸው ጉዳቶች ሲደርሱ መቆየታቸውን ነዋሪዎቹ ገልጸዋል፡፡

ባለፈው ክረምት ነዋሪዎቹ ከአንድ ኪሎ ሜትር በላይ በእግራቸው ለመጓዝ በመገደዳቸው፣ በሚደርስባቸው የመውደቅ አደጋ የመሰበርና ከሥራ የመቅረት፣ ልጆችም ከትምህርት ቤት የመቅረትና የመሳሰሉት ችግሮች ሲፈራረቁባቸው እንደከረሙ አስታውሰዋል፡፡

ቱቦ ለመቅበርና የተለያዩ ዓይነት ግንባታዎች ለማከናወን በሚል ተቆፍረው የተተዉ ጉድጓዶች፣ ርቀት እንዳላቸውና አደገኛ መሆናቸውን የሚጠቁም ምንም ዓይነት ምልክት ስላልተቀመጠባቸው፣ ከመሰበርና አካል ማጉደል ባለፈ የሰው ሕይወት እያጠፉ መሆናቸውን ነዋሪዎቹ ገልጸው፣ የሚመለከተው የመንግሥት አካል መፍትሔ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል፡፡

ነዋሪዎቹ የሚያነሳቸውን ችግሮችና ሕይወቱ አለፈ ስለተባለው ግለሰብ ማብራሪያ የሰጡት የአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ፈቃደ ኃይሌ፣ አደጋው መድረሱን አረጋግጠው ኮንትራክተሩና አማካሪ ድርጅቱ፣ በአደገኛና በተከለከሉ ቦታዎች አካባቢ ነጭና ጥቁር፣ ቀይና ነጭ ምልክቶች ማድረግ እንደነበረባቸው እየተነጋገሩ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ስለተፈጠረው አደጋ ከአማካሪው ድርጀት ዩኒኮን (ዩናይትድ ኮንሰልቲንግ ኢንጂነርስ) ጥያቄ የቀረበላቸው አንድ ኃላፊ፣ አደጋው ከምሽቱ አራት ሰዓት መድረሱን አረጋግጠው ምልክት ማድረጋቸውን፣ ችግሩ እንዴት እንደተፈጠረ እንዳልገባቸውና በመንገድ ሥራው ምክንያት ለሚደርስ አደጋ ግን ሙሉ ኢንሹራንስ እንዳለ አስታውቀዋል፡፡

ከጀነራል ዊንጌት እስከ አስኮ የሚሠራው መንገድ 2.5 ኪሎ ሜትር ርቀትና 30 ሜትር ስፋት አለው፡፡ ባለፈው ዓመት ጥር ወር የእስራኤሉ ኩባንያ መንገዱን ለመሥራት የ190 ሚሊዮን ብር ኮንትራት ከባለሥልጣኑ ጋር መፈራረሙ ይታወሳል፡፡ በዚህ ዓመት መጨረሻ አካባቢም እንደሚጠናቀቅ ይጠበቃል፡፡   

No comments:

Post a Comment