Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Wednesday, October 24, 2012

ኦህዴድ ለአራት ለመሰንጠቅ ጫፍ ደርሷል

ከአቶ መለስ ዜናዊ ሞት በኋላ በተደጋጋሚ ተሰብስቦ መግባባት ያልቻለው ኦሮሞ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት /ኦህዴድ/ በአራት ቡድን ተከፍሎ ውዝግብ ውስጥ እንደገባ የውስጥ አዋቂ ምንጮች ገለፁ፡፡ ለፓርቲው ቅርበት ያላቸው የፍኖተ ነፃነት ታማኝ የዜና ምንጮች እንደሚያረጋግጡት ኦህዴድ በአሁኑ ጊዜ በግልጽ ለአራት ቡድኖች ተከፍሏል፡፡ 

ቡድኖቹ 1ኛ ኦህዴድ- መለስ 2ኛ ኦህዴድ-አባዱላ 3ኛ ኦህዴድ- ኦሮሚያ 4ኛ ኦህዴድ- አድፋጭ  በሚል የሚታወቁ ሲሆን፣ የተካረረ ፍጥጫ ውስጥ የመግባት አዝማሚያ ታይቶባቸዋል፡፡ ንጮቻችን እንደሚያስረዱት “ኦህዴድ- ለመለስ” የሚባለው ቡድን ከህውሓት ጋር የቀረበ ግንኙነት ያለውና “ከመለስ ራዕይ ውጪ ምንም ዓይነት ሐሳብና እንቅስቃሴ ማድረግ የለብንም” የሚል ክርክር በማንሳት ኦህዴድ ውስጥ የተጀመረውን የስልጣን ይገባኛል ጥያቄ እንዲጠፋ ጥረት የሚያደርግ ነው፡፡


“የመለስ እቅድ” ሳንሸራርፍ መተግበር አለብን ብለው ራሳቸውን ያሳመኑት የዚህ ቡድን አባላት ከዚህ ሐሳብ ውጪ የሚያስቡትን እንደ ከሐዲ የሚፈርጁ ናቸው፡፡ በዚህ ቡድን ውስጥ ሙክታር ከዲር፣ ኩማ ደመቅሳ፣ አስቴር ማሞና ዘላለም ጀማነህ እንደሚገኙበት የዜናው ምንጮች ተቁመዋል፡፡
 
ሁለተኛው ቡድን “ኦህዴድ -አባዱላ” የሚባል ሲሆን የአባዱላን ወደ ክልሉ ፕሬዝዳንትነት ለመመለስ ከመጣር ውጪ ከመጀመሪያው ቡድን ጋር መሰረታዊ የሀሳብ ልዩነት የለውም፡፡ “ኦህዴድ ከዚህ  ቀደም እንደነበረው ከኢህአዴግ/ ህውሓት የሚሰጠውን መመሪያ እየተቀበለና እያስፈፀመ መቀጠል አለበት፡፡ በድርጅት ስምና በኦሮሞ ህዝብ ስም የፌደራል ስልጣን መጠየቅ ከድርጅቱ ዓላማ መውጣት ነው፡፡

 ክልላችንን እስካስተዳደርን ድረስ ለፌዴራል ሥልጣን መጨነቅ የለብንም፡፡ ከህውሓት ጋር ግጭት
ውስጥ መግባት የለብንም” የሚሉት የቡድኑ አባላት ውስጥ ውስጡን ግን ኦህዴድ በፌደራል ደረጃ ተገቢውን ውክልና ባለማግኘቱ የተነሳውን ተዋውሞ በተወሰነ ደረጃ የመቀበል አዝማሚያ ይታይባቸዋል፡፡ በዚህ ቡድን ውስጥ አፈጉባኤ አባዱላ ገመዳና የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር አለማየሁ ተገኑ እንደሚገኙበት ምንጮቻችን አስረድተዋል፡፡

ኦህዴድ- ኦሮሚያ የሚባለው ቡድን “ኦህዴድ የኦሮሞን ህዝብ መብትና ጥቅም ማስከበር አለበት፡፡ ድርጅቱ ከህውሃት ጥገኝነት መላቀቅ ያለበት ሰዓት ላይ ደርሷል፡፡ ድርጅቱ በአማራ ህዝብ ላይ እንዲከተል የሚደረገው የጥላቻና የብቀላ ፖለቲካ ማቆም አለበት፡፡” የሚል ሀሳብ ይዞ የሚሟገት ሲሆን የኦህዴድ ተጠሪነትም ሆነ አገልግሎት ለአሮሞ ህዝብ ብቻ መሆን ይጠበቅበታል፡፡ በድርጅቱ ውስጥ የህውሓት ተላላኪ የሆኑትን ግለሰቦች ከአመራርነት ማስወጣት አለብን፡፡ የሚል ጠንካራ
አቋም የሚያራምድ ቡድን ነው፡፡ 

“የኦሮሞ ህዝብ በፌዴራል ደረጃ ተገቢውን ውክልና ማግኘት አለበት፡፡” የሚሉት የቡድኑ አባላት መካከለኛውንና ወጣት አመራሮችን ድጋፍ ማግኘት የቻሉ ሲሆን የድርጅቱን መካከለኛ ካድሬዎች ሀሳብ ወደ አመራሩ እዳመጡ ምንጮቻችን አስረድተዋል፡፡ ከመካከለኛውና ወጣት አመራሩ ውጭ አቶ አለማየሁ አቶምሳና አቶ ጁኔዲን ሳዶን ጨምሮ ሌሎች የድርጅቱ ጠንካራ አመራሮች በዚህ ቡድን ውስጥ እየተሰባሰቡ መሆናቸውን ለማወቅ ተችሏል ፡፡
 
አራተኛው ቡድን “ኦህዴድ- አድፋጭ” የሚባለው ሲሆን አቋማቸውን በግልፅ ያላወጡና ወደ አሸናፊው ቡድን ለመቀላቀል ያደፈጡ አባላትን የያዘ ቡድን እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡ የቡድኑ አባላት በተለያዩ ክርክሮች ላይ አቋም ወስደው ከመከራከርና ከመጋጨት ይልቅ እያንዳንዱን ጉዳይ አጐንብሰው ለማለፍ ሞክረዋል የሚባሉት በዚህ ቡድን አባላት የኦሮሚያ ም/ፕሬዝደንት አቶ አብዱላዚዝ ዮሱፍ፣ ግርማ ብሩ፣ የኦህዲድ መስራቹ ጌታቸው በዳኔን ያካተቱ መሆናቸውን
ምንጮቻችን አብራርተዋል፡፡
 
ኦህዴድ በቅርቡ ማዕከላዊ ኮሚቴው ከሳምንት በላይ ስብሰባ ላይ ቆይቶ ስብሰባውን ቢያጠናቅቅም አሁንም ስብሰባው አዳማ ላይ ለመቀጠል ተገዷል፡፡ የአሁኑ ስብሰባ የዞንና የወረዳ አመራሮችን የየቢሮ ኃላፊና ም/ ኃላፊዎችን ባካተተ መልኩ ተጀምሮአል፡፡ በከፍተኛ ሙስናና የአስተዳደራዊ በደል የሚታወቁት የከተማ ከንቲባዎች የወረዳና የዞን አመራሮች በዚህ ስብሰባ ተካተዋል፡፡ 

በየአካባቢያቸው በበርካታ ወንጀል የሚጠረጠሩት የአካባቢ ኃላፊዎች በግምገማ ላይ ይገኛሉ፡፡ የዜና ምንጮቻችን እንደሚሉት ኦህዴድ እንደ ድርጅት ለመቆም ወይም ለመሰነጣጠቅ ወሳኝ ምዕራፍ ላይ ደርሷል ፡፡

No comments:

Post a Comment