Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Wednesday, October 24, 2012

የቃሊቲና ቂሊንጦ ወህኒ ቤቶች ገመና

ከኢንጂባራው ዘላለም
ውድ አንባቢያን፣ ባለፈው ፅሁፌ ላለፉት ዓመታት የገጠሙኝን የእስር ቤት ገመናዎች ከብዙ በጥቂቱ ዋና ዋና ነጥቦችን እንዳስቃኘኋችሁ የሚታወስ ነው፡፡ ስለ ሸዋ ሮቢት ወህኒ ቤት ላስጐበኛችሁ ቃል ገብቼ ነበር፡፡ ሆኖም ግን ደጋግሜ ሳስበው ስለቃሊቲና ስለ ቂሊንጦ ማረሚያ ቤቶች ለአንባቢያን ያስተላለፍኩት መልዕክት በቂ መስሎ ስለአልታየኝ እንደገና መፃፉን  መረጥኩኝ፡፡

 ለዛሬ ደግሞ ባለፈው ፅሑፌ በፍሬ ሃሳብ ደረጃ ብቻ የጠቀስኩትን በፌዴራል ማ/ቤቶች አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮችና የገዥው መደብ አባላት በሆኑ መኮንኖች የሚፈፀመውን ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት፣ የስልጣን መባለግና ውንብድና እንዲሁም የነኝህ ግለሰቦችም ሆነ የስርዓቱ አባላት ስብእና እስከ ምን ድረስ እንደሆነ እንደ ማሳያ ሊቀርብ የሚችል እውነታ ይዤ ቀርቤያለሁ፤ መልካም ንባብ፡፡

በመሠረቱ በወይኒ ቤቱ (ማ/ቤቱ) የሚገኙ ከፍተኛ መኮንኖችም ሆኑ አጠቃላይ በፌዴራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር ከፍተኛ የአመራር ቦታዎች ላይ የሚገኙ የሥርዓቱ ታማኝ ከፍተኛ መኮንኖች የተሸከሙትን ማእረግ ሆነ ኃላፊነት መሸከም የማይችሉ እና ለለበሱት ማዕረግ የማይመጥኑ ናቸው፡፡ እያንዳንዱን የሥልጣን እርከን ለመቆናጠጥ የብዙ ንፁህ ኢትዮጵያውያን ህይወት ገብረውና በብዙ ሚስኪኖች ደም እጃቸውን የታጠቡ በመሆኑ እያንዳንዱ  ንቅስቃሴያቸውም ሆነ አስተሳሰባቸው ይህን ሲፈፅሙ የኖሩትን ወንጀል ሚስጢራዊነት ከመጠበቅ አንፃር የተቃኘ ነው፡፡

በተጨማሪ የገዥው ሥርዓት ጐሰኛ የሆነ የስነ አስተዳደር ፖሊሲ አስተሳሰብ የተጠናወታቸው ከመሆኑም ሌላ ለለበሱት ዩኒፎርም ለለበሱት ማእረግ እንዲሁም ዛሬ ለሚዘምሩለት የትላንቱ ትግል ዓላማ ክብርም ግንዛቤም የሌላቸው ናቸው፡፡ ለዚህ ደግሞ ዋንኛ መገለጫው መኮንኖቹ የሚፈፅሙት ከተራ የሌብነት ተግባር አንስቶ እስከ ከፍተኛ የሙስና ቅሌቶች አንዱ ነው፡፡ ከገዥው ስርዓት የተለየ አመለካከትና አስተሳሰብ ያለውን ማንኛውንም ኢትዮጵያዊ እንደ ውጭ ጠላት ቆጥሮ ሲጨፈጭፉ የሚኖሩና በመጨፍጨፍ ላይ ይገኛሉ፡፡ በተጨማሪ ልዩነትን የሚያስተናግደው አስተሳሰባቸው የትምክህትና የጐሰኛነት አስተሳሰብ ተደምሮበት እስር ቤቶቹን ወደ መግደያና ማጐሪያ ስፍራነት ቀይሮታል፡፡

ከላይ ለመጥቀስ እንደ ሞከርኩት በቃሊቲና በቂሊንጦ ወይኒ ቤቶች በመንግስት አመራር ማረሚያ ቤቶች በተዋረድ ከላይኛው የሥልጣን እርከን እስከታች የተቀመጡትን ባለ ስልጣናት ምንነትና ማንነት አስቃኛችኋለሁ፡፡ የቃሊቲ ወይኒ ቤት የተመሠረተው እ.ኤ.አ 19 97 ዓ.ም በክረምት ወራት ሲሆን ከዛ ቀድሞ በአሁኑ ሰዓት የአፍሪካ ህብረት ዋና መስሪያ ቤት ያለበት በቀድሞ ስሙ ዓለም በቃኝ ወይኒ ቤት እየተባለ ከሚጠራው እስር ቤት የነበረው እስረኛና ጠባቂ ፖሊስ ሙሉ በሙሉ ወደ ቃሊቲ በተዘዋወረበት ወቅት ነበር፡፡

ከዛ ቀድሞ በነበሩት ብዙ አመታት በዓለም በቃኝ ወይኒ ቤት የእስረኛ አስተዳደርና የሰብአዊ መብት አያያዙ ጥሩ ካለመሆኑ ጋር ተያይዞ በተለያየ ጊዜ በፖሊሶችና በእስረኛው መካከል በተነሳ ግጭት ተከትሎ ለእስር ቤቱ አመፅ በመነሳቱ ከ19 በላይ የሚሆኑ እስረኞች ተገድለዋል፡፡ ነገር ግን ከዚያን ጊዜ በኋላ በዋነኝነት በዓለም በቃኝ እስር ቤት የተከሰቱ ግጭትና ግድያ ዋነኛው በ1995 የተከሰተው ነው፡፡ በዚህ ወቅት አጠቃላይ በማማ ላይ ካሉ ፖሊሶች በተተኮሰ ጥይት እና ኋላ ስማቸው እየተጠራ ወጥተው ባዛ የቀሩ እስረኞች ከ40 እስከ 50 ይሆናሉ፡፡
ይህንን ግድያ ከፈፀሙት መካከል ዛሬም በስራላይ ያሉ ሲሆን ድርጊታቸው እንደ ጀብዱ ሥራ ተቆጥሮ እስከ እንስፔክተር የደረሱ አሉ፡፡ ኢንስፔክተር ከእነዚህ ውስጥ በቂሊንጦ ወይኒ ቤት ሃላፊ ሆኖ በመስራት ላይ ይገኛል፡፡ (ዞን ማለት በእስር ቤቱ ከሚገኙ የእስር ግቢዎች አንዱን ይወክላል) ይህን ግለሰብ እንደ ማሳያ አነሳሁ እንጂ በወቅቱ ጭፍጨፋ ላይ ከተሳተፉት ከ10 በላይ አመራሮች ዛሬም በተለያዩ የስልጣን እርከን ላይ ይገኛሉ፡፡ ወደ ቃሊቲ እንመለስና ነገሮች እየከፉ የመጡት ከመጀመሪያውነው ምክንያቱ ደግሞ የቃሊቲ ወህኒ ቤት በራሱ የተመሰረተው ምርጫ 97 በኋላ የነበረውን ግርግር ተከትሎ በመሆኑ ነው፡፡

በሆነውም ባልሆነውም እያሳበቡ እስረኛውን አውጥቶ መደብደብና ማሰቃየት በሰንሰለት ማሰር እየበረታ መጣ በተለይ በወቅቱ በእስር ቤቱ ከፍተኛ ቁጥር የያዙትና መከ1984 ዓ.ም ጀምሮ በእስር ላይ ያሉ የኦነግ አባላትና ምርጫ 97ን ተከትሎ እየተለቀሙ የቅንጅት አባላትና ደጋፊዎች በመሆናቸው አብዛኛው እስረኛ የጥቃቱ ሰለባ ሆነ፡፡ በ1998 ዓ.ም በቃሊቲ አስከፊ ጭፍጨፋ ተፈፀመ፡፡ በቃሊቲ እስር ቤት ዞን 2 የተጀመረው ጅምላ ተኩስ ከመቅስፈት ወደ ዞን 3 እና ሌሎችም ሲስፋፋ ሁለት ሰዓት ባልሞላ ርሽና ከዞን ሁለት 86 ሰው ሲገደል እና ከ50 በላይ ሲቆስል በአንፃሩ በሌሎች ዞኖች የተወሰነ ወጣት ህይወት ጠፍቷል፡፡ 

የሚያሳዝነው ደግሞ ከሟቿች መካከል ታማሚዎች፣ በእንቅልፍ ላይ የነበሩ ፀጉር ቤት ፀጉር  ሲስተካከሉ የነበሩ ይገኙበታል፡፡ እጅግ የሚያስገርመው ደግሞ ጭፍጨፋው በተፈፀመ ዕለት ማታ ETV ሁለት ሰዓት ላይ በነበረው የዜና እወጃው ከቃሊቲ ማ/ቤት ሊያመልጡ የሞከሩ ሌቦች ክራውን ሆቴል ጀርባ 7 ሰው መገደሉን መዘገቡ ነበር፡፡ በወቅቱ የነበረው የሃገሪቱ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ከሰማንያ በላይ እሬሳ በቪዲዮ ቀርፆ ቢወስድም ከ50 በላይ ቁስለኞች ህክምና ሳይሰጣቸው ግቢ ውስጥ ዝናብና ሐሩር ሲፈራረቅባቸው ባይናቸው ተመልክተው ቢሄዱም በዚህ ጉዳይ ላይ አንዲትም አስተያየት ሲሰጡ አልተደመጡም፡፡ የኢፌዴሪ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን በአዋጅ የተሰጠውን ኃላፊነትና ተግባር በአግባቡ የማይወጣ ተቋም የሆነበትና በታሪኩ ጥቁር ነጥብ ያስመዘገበበት ነው፡፡
በወቅቱ የተረሸኑት እስረኞች አስከሬን በጅምላ መቃብር ተቀብሮ በጊቢ ውስጥ ሁለት ቦታ ላይ ይገኛል፡፡ ማንም ይህን እውነታ ማረጋገጥ የሚፈልግ ኢትዮጵያዊ በወቅቱ በቃሊቲ የነበሩ ከ4500 በላይ እስረኞች ዛሬም በዝዋይ፣ ቃሊቲና ቂሊንጦ ስለሚገኙ በፈለገው መንገድ ማጣራት ይችላል፡፡ ይህን ተከትሎም በወይኒ ቤቱ አዲስ ወይም ቀድሞ ከነበረው የከፋ የጥበቃ ስራዓት ተግባራዊ ተደረገ፡፡ ይኽውም አዳዲስ ጭለማ ቤቶች ከ8 በላይ የሆኑ እያንዳንዳቸው ከ3 ክፍል ድረስ ያላቸው ቤቶች ተሰሩ በተጨማሪ በየማማው ስር አንድ ሰው በአግባቡ የሚያስተኙ የቅጣትና የማሰቃያ ቦታዎች ተዘጋጁ፡፡ ይህ የሆነው በሁለት ዋንኛ ምክንያቶች ሲሆን አንደኛ የተፈፀመውን ወንጀል ሚስጥራዊነት ለመጠበቅ ሁለተኛ ለበቀል፡፡
ጭለማ ቤቶቹ ከመገንባታቸው በተጨማሪ በነዚህ ጭለማ ቤቶች ለጥበቃም ሆነ ለድብደባ የሚመደብ
የጥበቃ ቡድን የተመሰረተ ሲሆን ይህ ቡድን በአንድ ጨካኝ ግለሰብ የተባለ ግለሰብ የሚመራ ሆኖ አጠቃላይ አባላቱ ትግርኛ ተናጋሪ ሲሆኑ በ1998 ጭፍጨፋ የተሳተፉ መኮንኖች የሚመሩት ሁኖ ተዋቀረ፡፡ ይህም አንደኛ የመደብደብም ሆነ የማሰቃየት መመርያ ሲሰጣቸው ያለመንገራገር እንዲፈፀም፤ ሁለተኛ ለሚፈፀሙ በደሎች ሚስጥራዊነት (ምስጢር ለመጠበቅ) ምቹ ሁኔታን ፈጠረ፡፡

 እነኚህ የጭለማ ቤቶች እንደተገነቡ ወደነዚህ ጭለማ ቤቶች የመግባት እጣ የገጠማቸው አቶ ስዬ አብርሃ አቶ ታምራት ላይኔ፣ አቶ ሙኒር የሱፍ፣ መስፍን ኢታና ቴዲ አፍሮ (ቴድሮስ ካሳሁን) ከፍያለው ተፈራ አቶ ሙሉነህ ኢዩኤል አንዱዓለም አራጌ እና ሌሎችም ታዋቂ ሰዎች የሚገኙበት ነበር፡፡ አብዛኛውን ቁጥር የሚይዙት ግን የቅንጅት አባላት የነበሩና ከተለያየ አካባቢ የኦነግ አባላት ናቸው እየተባሉ የታሰሩ ናቸው፡፡ አቶ ስዬ በመጽፋቸው ለምን እንዳልዘረዘሩት ገርሞኛል፡፡
በ-------------- ወር ደግሞ አዲስ ነገር ተከሰተ ኢህአዴግ ከ40 በላይ የሆኑ የአማራ ተወላጆችን ሰብስቦ አሰረ፡፡ የእስራቱ መንስኤ ደግሞ የግንቦት 7 አባል ናቸው የሚል ነበር፡፡ ከታሰሩትም ሰዎች መሀከል ወታደራዊ ጄነራሎእና ከፍተኛ መኮንኖች ይገኙበታል፡፡ ከታሰሩበት ወቅት ጀምሮ በማዕከላዊ የተለየ ጥበቃና ምርመራ ሲከናወንባቸው ቆይተው ፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ከቀረቡ በኋላ በቀጥታ ወደ ቃሊቲ በመምጣታቸው ምክንያት በቃሊቲ የነበረው ኑሮ ከድጡ ወደ ማጡ ወረደ፡፡ በቃሊቲ ያሉ ጭለማ ቤቶች በሙሉ በአዲስ መልክ ጥበቃ ተመደበላቸው፡፡ በነዚህ ጭለማ ቤቶች በጥበቃ የተመደቡ የጥበቃ አባላት በሙሉ ትግርኛ ተናጋሪ እንዲሆኑ ተደረገ፡፡

 ተመርጠው የሚመሩት ቡድን በእስር ቤቱ ያሉ ጭለማ ቤቶችን ይቆጣጠራል፤ይደበድባል፤ በሰንሰለት ያስራል ወዘተ እኚህ ተከሳሾችም ከማእከላዊ እንደ መጡና ክሳቸው በፍርድ ቤት የመታየት ላይ እያለ እንደ ማንኛውም እስረኛ ዞን 3 (የቀጠሮ ዞን) መቆየት ሲገባቸው ልክ እንደ መጡ ወደነዚህ ጭለማ ቤቶች ተጋዙ፡፡ በተለይ ጄነራል ተፈራ ማሞ፣ ጄነራል አሳምነው ጽጌ፣ ኮረኔል ደምሰው አንተነህ፣ ሻለቃ መኮንን ወርቁ የተባሉ 2x2 በማይሆኑ ጠባብ ክፍሎች ውስጥ ለብቻቸው እንዲታሰሩ ተደረገ፡፡ ይህም ከሆነ በኋላ እነኚህ ተከሳሾች ከቤተሰብ ጋር መገናኘት ቢፈልጉም ሆነ ህክምና ማግኘት ቢፈልጉ ቀድሞ በተቋቋመውና ለጥበቃ በተመደበው ቡድን እና በነየ በጐ ፍቃድ ብቻ ይከናወናል፡፡
ከዚህ በዘለለ የመብት ጥያቄ መጠየቅ በተለይ ከግል ጠበቃ ጋር መገናኘት የማይታሰብ ሆነ፡፡ አስከፊው ነገር ደግሞ እኚህ ተጠርጣሪዎች ፍርድ ቤት ቀርበው ስለመብታቸው ጥያቄ በሚያቀርቡበት ወቅት ወደ ወይኒ ቤቱ ከተመለሱ በኋላ ፍርድ ቤት በህግና በዳኞች ፊት ባቀረቡት ጥያቄ ምክንያት ለሊት ድብደባ ይፈፀምባቸው ነበር፡፡ ለአብነት ይህል ጄነራል ተፈራ ማሞና ሻለቃ መኮንን ወርቁ በተደጋጋሚ ለድብደባ ተዳርገዋል፡፡ ድብደባውን የሚፈፅሙት ከላይ ስማቸው የተጠቀሱት ለድብደባ ያዘጋጁት ቡድን ሲሆን እነኚህ ፖሊሶች ይህን ግፍና በደል ለመፈፀማቸው በህግ መጠየቅ ሲገባቸው የፈፀሙት ወንጀል መሪዎቻቸውን ለማስደሰት የተበረከተ ገፀ በረከት ስለሆነ በተቃራኒው ስልጣን ተጨምሮላቸዋል፡፡
በነዚህ ጭለማ ቤቶች የተሰቃዩና በመስቃየት ላይ የሚገኙት ከላይ የተጠቀሱት ብቻ ሳይሆኑ እነኚህ ለአብነት ተጠቀሱ እንጂ ለምሳሌ እነ ኢንጅነር መስፍን አበበና ኢንጅነር ተስፋሁን ጨመዳ የተባሉ የኦሮሞ ተወላጆች ከኬንያ ታፍነው ከመጡበት ጊዜ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ጭለማ ቤቶች ለየብቻ ታስረው ድብደባና እንግልት እየተፈፀመባቸው በመኖር ላይ ይገኛሉ፡፡ የዚህ ወንጀለኛ ቡድን ተግባር ይህ ብቻ አይደለም፡፡ ይህ ቡድን በቀጥታ ከስርዓቱ መረጃና ደህንነት መሪዎች መመርያ እየተቀበለ ያስፈፅማል፡፡ በመሰረቱ የኢህአዴግ የማሰርያና የመግረፊያ ቦታዎች ቃሊቲና ማእከላዊ ብቻ አይደሉም፡፡ 

በአሁኑ ሰዓት አድራሻቸውን መጥቀስ አስፈላጊ ያልሆነ የሥርዓቱ መረጃና ደህንነት ቢሮ  የሚጠቀምባቸው ከ7 ያላነሱ ቪላ ቤቶች በከተማ ውስጥ የሚገኙ ሲሆን ማንኛውም ፖለቲከኛ ወይንም በነርሱ ቋንቋ ሽብርተኛ ተብሎ የተጠረጠረ ግለሰብ ሲታፈን ተሸከርካሪ ውስጥ ከገባ በኋላ አይኑና እጁ ታስሮ ወደ እነዚህ ቪላዎች ይወሰዳል፡፡ በመቀጠልም አስፈላጊ ነው ተብሎ የታመነበት ነገር ሁሉ ከተፈፀመበት በኋላ በህይወት ከተረፈ ወደ ማእከላዊ ይወሰዳል፡፡ ወደ ተነሳሁበት የእስር ቤት አጀንዳ ልመለስና በየወይኒ ቤቶቹ ያሉት መኮንኖች የፈፀሙት በደልና ግፍ ተቆጥሮ (ዘርዝሮ) ለመጨረስ ብዙ ግዜ ያስፈልጋል፡፡ ከላይ ስነሳ እንደ ጠቀስኩ በየወይኒ ቤቱ ያሉ መኮንኖች አንዱ ሲሰርቅ አንዱ ሲዘርፍ ሌላው ሲገርፍና ሲያንገላታ ሃይባይ የጠፋበት ሁለት ዋና ዋና ምክንያቶች አሉት፡፡
2 እያንዳንዱ ከተራ አባል እስከ ከፍተኛ አመራር ያለ በንፁህ ኢትዮጵያዊ ደም እጁን የታጠበ በመሆኑ አንዱ ሌላውን የመቃወምም ሆነ የመገሰፅ ሞራል የለውም፡፡ አሊያም አይፈልግም፡፡ 2 ከጅማሮ ይዘውት የመጡት የዘረኝነትና ከደም ጋር የተቆራኘው አስተሳሰባቸው ሌላውን ሌላውን ኢትዮጵያዊ እንደ ጠላት እንዲቆጥሩት ስላስገደዳቸው ሀገር ማለት እነሱ ብቻ ህገ መንግስት ማለት መለስ ዜናዊና የመለስ ዜናዊ ፍላጐት አድርገው ያስባሉ፡፡ ይህ በመሆኑም ከነርሱ ፍላጐትና ስልጣን የሚወጣ ማንኛውም አካል ይጠፋል፡፡ ሙስና በቃሊቲ ይህን በዚህ ልቋጭና በመቀጠል በቃሊቲ የሚፈፀሙና በመፈፀም ላይ ስላሉት ተራ ሌብነቶች አንስቶ እስከ ከፍተኛ የሙስና ወንጀሎች እንዲሁም ብልሹ አሰራሮች በመጠኑ ላመላክታችሁ፡፡

በየማረሚያ ቤቶቹ የሚፈፀሙት የሙስናና የሌብነት ተግባራት ምንጫቸው 3 ሲሆኑ እነርሱም 1ኛ መንግስት ለእስረኛውና ለእስር ቤቶቹ የሚመድበው ገንዘብ 2ኛ እስረኛው ተከራይቶ  ሚገለገልባቸው የተለያዩ የመዝናኛና የመገልገያ ዘርፎች 3ኛ ለእስረኛው ያልተፈቀዱ ነገሮችን በማድረግ ወይም ከከሳሽ ሀብታሞች ገንዘብ በመቀበል የእስረኛውን መብት በመጣስ የሚፈፅሙ ናቸው፡፡ እነኚህን ከላይ የተጠቀሱ ዋናዋና ነጥቦች ስንመለከት በፌዴራል ማረሚያ ቤቶች ስር የሚገኙ ማረሚያ ቤቶች በተለይ ቂሊንጦ ቃሊቲ ዝዋይና ድሬደዋ ማረሚያ ቤቶች እጅግ ሲበዛ ተቆጣጣሪ የሌላቸውና ማንኛውም ነገር በግልሰቦች በጐ ፍቃድ የሚከናወንና የሚተዳደር ነው፡፡
የድሬደዋ፣ ዝዋይ፣ ሸዋሮቢትና ቃሊቲ ማረሚያ ቤቶች ላለፉት ብዙ አመታት ከ4 የማይበልጡ ኋላፊዎች እየተፈራረቁ ያስተዳደሩት ሲሆን በዚህም ለታራሚው ለምግብ አቅርቦት የሚመደበው ባጀት የሕክምና አገልግሎት መስጫ መሳርያዎችና መድሃኒቶች መንግስት እያቀረብኩ ነው ቢልም በነዚህ ማረሚያ ቤት የሚገኝ ቁጥሩ ከ18000-19000 የሚገመት ታራሚ (እስረኛ) የሚመገበውን ምግብ መሰል ነገርም ሆነ የሚሰጠውን የህክምና አገልግሎት ማየት የፈለገሰው ከእለታት አንድ ቀን ብቅ ብሎ መጐብኘት ይችላል፡፡ እስረኛው ለምግብ እጥረት ከመሰቃየቱ በላይ ለፅዳት የሚሆን ሳሙና እንኳ በወቅቱ ስለማይቀርብለት በብዛት ለህመም ይጋለጣል፡፡ 

በታመመለትም ወቅት ወደ ህክምና ለመቅረብ ያለው ቢሮክራሲ እንዲሁም በቂ የመድሃኒት አቅርቦትና የስለጠነ የሕክምና ባለሙያ በሌለበት ለህልፈተ ህይወት የተጋለጡ እስረኞች ቁጥር ብዙ ሲሆን እንደ አስፈላጊነቱ ስም ዝርዝራቸውን መግለጽ ይቻላል፡፡ በአንፃሩ ለህክምናና ለምግብ የሚመደበው በጀት የሚቆጣጠረው ካለ መኖሩም በበይ በተለይ በቃሊቲ ወይኒ ቤት በቀን ከ170-100 እስረኛ አዲስ ስለሚገባና ከተለያዩ እስር ቤቶች ከዝዋይ ቂሊንጦ፣ ድሬደዋ፣ ሸዋሮቢት እስር ቤቶች ከ500 የሚበልጡ እስረኞች ስለሚገቡና ስለሚወጡ በቀን የሚመደበው ወጪ ተለይቶ ስለማይታወቅ ለሙስና እጅግ በር የከፈተ ነው፡፡ 

በተጨማሪ በየ እስር ቤቶቹ ያሉ የፋይናንስ አስተዳደር አካላት ከላይ ጀምሮ በተዘረዘሩ ወንጀሎች በሙሉ የተሳተፉና የአንድ አይነት ጐሰኛ አስተሳሰብ ተከታዬች በመሆናቸው የመጠቃቀምና የእከክልኝ ልከክልህ ጨዋታ እጅግ ይበረክታል፡፡ ሁለተኛውና እጅግ የሙስና ምንጭ የሆነው ዘረፋ ደግሞ በማረሚያ ቤቶቹ የሚገኙ የመዝናኛና የአገልግሎት መስጫ መስኮ ገቢ ሲሆን ይህ ዘርፍ የተሌ የሚያደርገው ደግሞ ከሙስና ምንጭነቱ በተጨማሪ የዘረኝነት ጥቅም ማስጠበቂያና የዜጐች ምራል መግደያ ሆኖ ማገልገሉ ነው፡፡

 በቃሊቲ እስር ቤት ለእስረኛው ተከራይቶ አገልግሎት የሚሰጥ አስር የሻይ ቡና ክበባት አሉ፡፡ አንዱ ክለብ የሚከራይበት ዋጋ በወር ዝቅተኛው 11.000 (አስራ አንድ ሺ) ሲሆን ከፍተኛው 37.000 ነው፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት ደግሞ ይህንን ክበብ ተከራይቶ የሚሰራ ሰው የመስራት የውሃ፣ የታከስ ወጪ ስለሌለበትና የሠራተኛ ደሞዝ ከፍተኛው 80 ብር ሲሆን ከዚህ በተጨማሪ ጥራቱ እጅግ የወረደ ቡና ሻይ ወተት ቁርስ እጅግ ባልተመጣጠነ ዋጋ ስለሚያቀርብ ነው፡፡ በዝቅተኛ ዋጋ የሚከራየው የዞን አንድ ክበብ ነው፡፡ ከፍተኛው ዞን ሁለትና ሦስት ነው፡፡

አጠቃላይ በጊቢው 8 የወንድ ዞኖችና 2 የሴት ዞኖች ስለሚገኙ በወር ምን ያህል ገቢ ከክለብ እንደ ሚሰበሰብ መገመት ቀላል ነው፡፡ ከዚህ ሌላ ሌሎች የገቢ ምንጮች በየዞኑ በአማካይ 3 ከረንቡላዎች አሉ፡፡ የአንዱ ከረንቡላ ዋጋ በወር ከ850-1000 ብር ሲከራይ ሁለት ሁለት ቴኒስ መጫወቻ ያለ ሲሆን በየዞኑ የአንዱ ዋጋ ከ450-600 ብር ነው፡፡ በየወሩ ከተለያየ እደጥበብ ስራዎች ቀረጥ ከየዞኑ በወር በአማካይ ከ3500-5000 በየወሩ ይሰበሰባል፡፡ የሕብረት ሱቅ የሚገኝ ትርፍ በየዞኑ ከ6000 7500 ብር ይደርሳል፡፡
እንግዲህ እነኚህ ከላይ የተጠቀሱት የገቢ ማስገኛ ዘርፎች በእስር ቤቶቹ መተዳደርያ ህግ መሠረት እስረኛው እራሱ በሚመርጣቸው እስረኞች ተወካዮች ወይም አጠቃላይ ኮሚቴ አማካይነት የሚተዳደሩና የሚሰበሰበው ገቢ ለእስረኛው የተለያየ አገልግሎት የሚውሉ ናቸው፡፡ ለምሳሌ ለሕክምና፣ ለትምህርት፣ ለሕግ አገልግሎት ለምግብና አልባሳት ድጐማ ለሳሙና ምላጭና ሌሎች የመፀዳጃ መሳርያዎች ግዥ እንደሚውል ይደነግጋል ሆኖም ግን ለይስሙላ እስር ቤቱ የፈቀደውን ግለሰቦች እያደራጀና በነዚህ ሰዎች አማካይነት ይህን ገቢ የሚሰበስብ ሲሆን ከዚህም ለእስረኛው አገልግሎት እንዲሰጥ ገንዘብ ተመድቦ አይተንም ሰምተንም አናውቅም፡፡ እንግዲህ ይህ ከላይ የጠቀስኩት የገንዘብ መጠን በቃሊቲ ብቻ በወር የሚሰበሰብ ሲሆን በሌሎች እስር ቤቶችም
በተመሳሳይ ሁኔታ ይሰበሰባል፡፡

ሌላው ከሙስና ይልቅ አስከፊው ነገር ደግሞ ማንም ኢትዮጵያዊ የሆነ በነዚህ ክበቦች ሆነ ከረንቡላ አሊያም የህብረት ሱቅ አገልግሎት ለመስጠት በሚወጣው ጨረታ ተወዳድሮ ቢያሸንፍ መስራት ያለመቻሉ ሲሆን ምናልባት የአንደኛ ዜጐች እጥረት አጋጠመ በወቅቱ ያሸነፈ ግለሰብ ለነሱ (ለእስር ቤቶቹ አመራሮች) ጥቅም የማያጋራና ወሬ የሚያመላልስ ከሆነ እንዲስራ ይፈቀድለታል፡፡ ይህ ደግሞ አዲስ የባለጊዜዎቹ ሰው እስኪመጣ ብቻ ነው፡፡ ይህ ከላይ የጠቀስኩት እኩልነት ስለ ማስፈንና ስለ ኪራይ ሰብሳቢነት መጥፎነት ጠዋት ማታ ለሚዘምረው ኢህአዴግ ከፍተኛ መኮንኖች የሚፈፅሙት አሥነዋሪ ተግባር ነው፡፡ ሦስተኛው የገቢ ምንጭ በእስር ቤቱ ያሉ ባለ ሀብቶችና በእስር ቤቱ ያሉ ሀብታም ያሰራቸው እስረኞች ናቸው፡፡ ኢህአዴግ ባለፉት አመታት እጅግ በጣም ብዙ ሀብታሞችን ማሰሩ ለነዚህ ህጋዊ ሌቦች ጥሩ እድል ሆኖዋቸዋል፡፡ 

በተለይ አራጣ አበዳሪዎች የአዲስ አበባን መሬት ቸረቸሩ በሚል የታሰሩ የሪል ኢስቴት ባለቤቶች መዕንዲሶች ወርቅ ያጭበረበሩ ቅሸባ እንደ ታምራት ገለታ ያሉና ሌሎችም እንደ አጋጣሚ እነኚህ ግለሰቦች ሁለት አመት በማይሞላ ግዜ ተሰብስበው የታሰሩ በመሆኑ ከጥበቃ አንስቶ እስከ ከፍተኛ አመራር ሎተሪ የደረሳቸው ያህል ተደስተዋል፡፡ ከላይ ከተጠቀሱት በተጨማሪ በ100 ሚሊዬን የሚቆጠር ገንዘብ በልተዋል በሚል በሙስና የተከሰሱ በታክስና ቫት ማጭበርበር የተከሰሱ ጅምላ ነጋዴዎች አስመጪና ላኪዎች ይገኙበታል፡፡
በቃሊቲ ገንዘብ ስድስትና ከዚያም በላይ የስሜት ህዋስ ነው፡፡ ገንዘብ ያለውና ገንዘብ የሌለው እኩል አይታይም፡፡ ገንዘብ ያለው በሰበብ አስባቡ ታጅቦ ከተማ ሲመላለስና በየቀኑ ሪፈር በሚል ሰበብ እየወጣ ከሚስቱና ከልጆቹ ጋር ሲውል ገንዘብ የሌለው ግን ቢታመም አዛኝ የለው፤ ሪፈር ቢባል ነዳጅ የለም ወይም አጃቢ የለንም በሚል ተልካሻ ሰበብ ሕክምና ይከለከላል፡፡

ገንዘብ ያለው የግል ላፕቶፕ ኮንፒዩተር አስገብቶ ሲጠቀም፣ ሞባይል እንደ ልቡ ሲጠቀም፤ ጫት ዊስኪና የግል ዲቪዲ ሲገባላት ድሃው ግን ለቤተሰቡ ደብዳቤ ፅፎ እንኳን በሰንሱር ምክንያት ይህን ሰርዝ ይህን ቀንስ ይህ ማለት እንዲህ ሊሆን ይችላል እየተባለ ይሰቃያል፡፡ ገንዘብ ካለ በሰማይ መንገድ አለ እንዲሉ በቃሊቲ ገንዘብ ካለና ፖለቲካቸው ካልተነካ የተፈለገው ድርጊት ሁሉ ይከናወናል፡፡ ሀብታሙ ዊስኪ አስገብቶ ሲጠጣ ደሃው ንፁህ ውሃ ታሽጐ ቢመጣለት አይገባለትም፡፡

ሀብታሞቹ ይህን አገልግሎት በማግኘታቸው ለአፀፋው ቲንሽ ቤት ጀምሬ ቆርቆሮ አነሰኝ ቤት እንዳልሰራ ሲሚንቶ ተወደደ ወዘተ እየተባሉ በሚሰጡት ገንዘብ ከG+2 እስከ G+4 ቤት የገነቡ ሁለትን ሦስት ተሳቢ ኤሮትራከር የገዙ ከ5-19 ሚሊዬን ብር ባንክ ያስቀመጡ ከፍተኛ የፖሊስ መኮንኖች ሲኖሩ የነዚህ ሰዎች ወርሃዊ ደሞዝ ግን ከ2000 -30000 አይበልጥም፡፡ በዚህ የደሞዝ መጠን ልጆች አስተምሮ ቤተሰብ አስተዳድሮ በባንክ ቆጥቦ ለ5 ሚሊዬን ብር በላይ ማጠራቀም የማይታሰብ ነው፡፡ ከከፍተኛ መኮንኖቹ በታች ያሉ የዞን ተጠሪ (ኋላፊዎች) ያቅማቸውን ያህል የሚሰርቁ ሲሆን ይህም እንደ ሚከተለው ነው፡፡ አንድ እስረኛ ወደ ቃሊቲ እስር ቤት ሲገባ ከሚገጥሙት ፈተናዎች አንዱ እንደ ሰው ተቆጥሮ መኝታ የማግነት መብቱ ይነፈጋል፡፡ 

ይህ የሚሆነው ደግሞ ከላይ እንደ ጠቀስኩት በየዞኑ ኃላፊ ተብለው የተመደቡት የኢንስፔክተርና ከዛበታች ማእረግ በትከሻቸው ላይ የተሸከሙ የስርዓቱ ሎሌዎች ነውረኛ ተግባር ምክንያት ነው፡፡ ይህ ማለት እስረኛው ወደ እስር ቤቱ ሲመጣ እንደየ አመጣጡ ተገቢውን የመኝታ ስፍራ ማግኘት ሲገባው አልጋና የተሻለ የመኝታ ስፍራ ለማግኘት ከብር 500- 3000 ብር ይጠየቃል፡፡ ይህ የሚሆነው በየዞኑ ከመኮንኖቹ ጋር ተመሳጥረው (ተሻርከው) በሚሰሩ የእስረኛ አስተዳደሮች አማካይነት ሲሆን የሚሸጡትን አልጋ ገንዘብ ሰብስበው መንግስት ከኢትዮጵያ ህዝብ መቀነት ፈትቶና ገንዘብ ሰብስቦ ደሞዝ ለሚከፍላቸው መኮንኖች ሲያስረክቡ እንደየ ድርሻቸው ኮሚሺን ያገኛሉ፡፡
እነኚህ አልጋ የሚሸጡ እስረኞች አብዛኞቹ አንባቢዎቼ የምታውቃቸው ሲሆኑ ወታደር የነበሩ የባለሥልጣናትና የመንግስት ተቋማት የነበሩና በነበራቸው ኃላፊነትና በእጃቸው በነበረ መሣርያ ተጠቅመ የአዲስ አበባን ባለ ሀብት በመዝረፍ ያንገላቱና በሚሊዬን የሚቆጠር ገንዘብ ከባንክ የዘረፉ ናቸው፡፡ እስር ቤት ከገቡ በኋላም ለሚናገሩት ቋንቋ ተጠቅመው የእስረኛ አስተዳደር የእስረኛ ስነ ስርዓት አስከባሪ ወዘተ እየተባሉ እስረኛውን ሲጨቁኑና ሲያንገላቱ በአንፃሩ ከዩኒቨርስቲና ሁለተኛ ደረጃ የትምህርት ገበታቸው ኦነግ፣ አርበኛ ግንባር፣ ቅንጅት፣ ግንቦት ሰባት. . . እየተባሉ ታንቀው እስር ቤት የገቡ የኦሮሞና የአማራ ተወላጆች ያለ እዳቸው በየጭለማ ቤቱ ይማቅቃሉ፡፡
እንደገና ቃሊቲ ወህኒ ቤት ወደ ቀደመው ነገራችን እንመለስና በእያንዳንዱ ቀን ከ70-100 እስረና ወደ ቃሊቲ ወይኒ ቤት ከአሥሩም ክፍለ ከተማና ከማእከላዊ እንዲሁም ከአዲስ አበባ ፖሊስ ወንጀልና ትራፊክ አደጋ ምርመራ በተለምዶ ስሙ 3ኛ ፖሊስ ጣቢያ ይመለሳል፡፡ ከዚህም 90% የሚሆነው ሳይፈረድበት በቀጠሮ ወደ ቃሊቲ የሚመጣ በመሆኑ በቀጥታ ወደዞን 3 ይገባል (ዞን 3 ማለት በቃሊቲ ከሚገኙ ዞኖች ያልተፈረደባቸው በቀጠሮ ላይ ያሉ እስረኞ የሚቆዩበት ዞን ነው)፡፡

 ይህ በመሆኑም ዞን 3 ገብቶ አልጋ ማግኘት ወይም መሬት ተመቻችቶ መተኛት የማይታሰብ ነው፡፡ ገነት ካለ ግን አልጋ ላይ የነበረ እስረኛም ቢሆን ከአልጋ ወርዶ አዲስ ለመጣው ከፋይ እንዲሰጥ ይደረጋል፡፡ በተለይ የሚከፈለው ገንዘብ መጠን ከፍ ባለ ቁጥር እንክብባቤው ጥሩ እየሆነ ይመጣል፡፡ በአንፃሩ ደግሞ በየቀኑ ወደ ዞኑ የሚገባው የሰው ሃይል ከፍተኛ በመሆኑ ከመግቢያ በር እስከ መፀዳጃ (ሽንት ቤት) ድረስ ለመገላበጥ እንኳ በማይመች ሁኔታ በአንድ ጐን ተኝተው የሚያድሩ ድሃ ዜጐች ቁጥር የትየለሌ ነው፡፡ ይህ ሁሉ ፍጡር ጐኑ ታሞ ገሚሱ ተቀምጦ ሲያድር ግን ከ10-15 የማይንሱ አልጋዎች ለነገ ገቤ መጠባበቂያ ሲባል ባዶ ያድራሉ፡፡ ሌላው እጅግ የሚያስከፋው ጉዳይ ደግሞ ዛሬ ኢህአዴግ ሃገሪቱን ማስተዳደር ከጀመረ ከ21 አመታት በኋላም ኢትዮጵያዊ ከኢትዮጵያዊ የሚበልጥበት መስፈርት መኖሩ በንጉሱ ወይም በደርግ ዘመን ሳይሆን ዛሬ በኢህአዴግ ዘመን መሆኑን ለማወቅ ከፈለጋችሁ ቃሊቲን ማየት
ነው፡፡
አንድ በጣም የታመመና ሆስፒታል መተኛት የሚገባው ህመምተኛ ወይም ምርመራ ላይ ከመጠን በላይ ተደብድቦ መራመድ የማይችል እስረኛ ሌላ ጤነኛና ወጣት የሆነ ትግርኛ ተናጋሪ እኩል ቢመጡ ትግርኛ መናገሩ ብቻ ለትግሬው ቅድሚ ያሰጠዋል፡፡ አልጋ ወዲያው  ይሰጠዋል፤ ገንዘብ አይጠይቅም፤ በጊቢው ውስጥ በሌላ ኢትዮጵያዊ ተይዞ የነበረ የገቢ ማስገኛ ክበብ፣ ከረንቡላ፣ የህብረት ሱቅ እና ሌሎችም ተቀምቶ ይሰጠዋል፡፡ እንዲሁም ወደ እስር ቤቱ በመጣ በአጭር ቀን ውስጥ የእስረኛ አስተዳዳሪ ተደርጐ ይሾማል፡፡ ይህ ሁሉ ሲከናወን በእስር ቤቶቹ የተለመደ ተግባር በመሆኑ ጥያቄ የሚያነሳ የለም፡፡
ሌላው ጉዳይ ደግሞ መንግስት 24 ሰዓት ሙሉ ጥፋተኞችን የማስተማርና ብቁ ዜጋ የማድረግ ፖሊሲ እንደሚከተል በETV እየገለፀ ባለበት ወቅት ቃሊቲ ያሉ የፖሊስ መኮንኖች እስር ቤቱን የመጠጥና የጫት የሐሺሽ መነገጃ ማእከል በማድረጋቸው በህግ የሚጠይቃቸው አንድም ባለሥልጣን ወይም ህግ የለም፡፡ ይህ የሐሺሽና የሲጋራ ትንሽ ስለቂሊንጦ በቃሊቲ ብቻ የተወሰነ አይደለም እንደ ቃሊቲ ሁሉ በቂሊንጦና በዝዋይ እስር ቤቶች ይካሄዳል ለዛሬ ግን በጥቂቱ የቂሊንጦ ወይኒ ቤትን አስጐበኛችኋለሁ፡፡ የቂሊንጦ እስር ቤት ሶስት ዞኖች ያሉት ሲሆን በያንዳዱ ዞን ከ550-650 እስረኞች ይገኛሉ በአጠቃላይ በ3ቱም ዞኖች የሚገኘው እስረኛ ቁጥር ከ11750 በላይ ነው፡፡ አብዛኞቹ የቂሊንጦ እስር ቤት አመራሮች በሙሉ ከቃሊቲ ወደ ቂሊንጦ የተዘዋወሩ በመሆኑ የውንብድናውን ስራ ተክነውበታል፡፡ 

በቂሊንጦ የፈጠሩት የገቢ ምንጭ የተለየ ነው፡፡ በዚህም መላውን እስረኛ ሰብስበው ሲጋራ ለጤና ጠንቅ መሆኑን እና ከኢኮኖሚ አንፃርም ተቀባይነት የሌለው መሆኑን ካስረዱ በኋላ ሲጋራ ማጨስ እንዲቆም መወሰኑን ገልፀዋል፡፡ ይህ ሲሆን ግን መፃኢ እድላቸው ምን እንደሆነ ቀድመው የገመቱ እስረኞች ነበሩ፡፡ ከሣምንት በኋላ ሲጋራ እንደ ሚጀመርና 60 ሳንቲም የነበረውን ሲጋራ በ10 ብር እንደሚገዙ የገመቱ ነበሩ፡፡
የተገመተውም አልቀረም ሣምንት ሳይሞላ ቂሊንጦ ሲጋር እንደ ልብ ይጨስ ጀመር፡፡ የአንድ ሲጋራ ዋጋ ከ12-15 ብር የአንድ ፓኬት ሲጋራ ዋጋ (20 ፍሬ) ከ240-300 ብር ተሸጠ፡፡ ይህ ማለት አንድ ካርቶኒ ሲጋራ 6000 ወደ 100,000 እና ከዛ በላይ አደገ ማለት ነው፡፡ በቀን በአንድ ዞን ከሁለት ስቴካ በላይ ሲጋራ ይገባል፡፡ ይህ ደግሞ በ24 ሰዓት ከአንድ ዞን እስከ 3000 ብር ትርፍ ይገኛል ማለት ነው፡፡ አብዛኛው እስረኛ አጫሽ ነው የ60 ሳንቲም ሲጋራ በአሥር ብር እየገዛ ያጨሳል፡፡ ብቻውን ያልቻለ ለሁለት ለሦስት እየሆነ ያጨሳል ይህ ደግሞ በቀላሉ ለተላላፊ በሽታ እንዲዳረግ በር ይከፍታል፡፡ በአጠቃላይ እስረኛው ላይ በሚፈፀመው ብዝበዛ ማንም ደፍሮ የሚጠይቅ የለም፡፡ ቢኖር እንኳ የሚጠበቀው እድል እጁ በሰንሰለት ታስሮ ጭለማ ቤት ይወረወራል፡፡ 

አብዛኛው እስረኛ ለምን ሲጋራ አታቆምም ተብሎ ሊጠየቅ አልቻለም፡፡ ባይኖር አቆማለሁ ነገር ግን አጠገቤ እየተጨሰ እንዴት አድርጌ እተዋለሁ ይላል፡፡ እድለኛ የሆነ ደግሞ በሽያጩ ይሳተፋል፡፡ የእንጀራ ጉዳይ ስለሆነ አልፈረድበትም፡፡ ሆኖም ግን ወይ ቸባሬ መሆን አለበት፡፡ አሊያም ትግሬ ጓደኛ ሊኖረው ይገባል፡፡ የከፋው ነገር ደግሞ ሲጋራውን አስገብተው የሚሸጡት መንግስት በኃላፊነት መድቦ ያስቀመጣቸው ኃላፊዎች መሆናቸው ነው፡፡ ከዚህ መስመር ውጭ ያለ ማንኛውም አካል ቢያደርገው አይደለም ቢያስበው አበቃለት፡፡
ለአብነት ያህል በግንቦት ወር 2004 ዓ.ም ተመስገን አበበ የተባለ እስረኛ እና ተክላይ የተባለ የጥበቃ አባል የሆነ ፖሊስ ሲጋራ ሲቀባበሉ ተያዙ ተብለው ተመስገን አበበ የተባለው እስረኛ በአስከፊ ሁኔታ ተደብድቦ በሰንሰለት ሲታሰር ተክላይ የተባለው ፖሊስ እንደ ህፃን እጁ ወደኋላ ታስሮ ከተገረፈ በኋላ ከስራ ተባሯል፡፡ ይህን እውነት ማንኛውም አካል ወደ ቂሊንጦ መጥቶ ተመስገን አበበን አሊያም በወቅቱ ተጠርጥሮ የተደበደበውን እስጢፋኖስ ኃይሉን ማነጋገርና እውነታውን መረዳት ይችላል፡፡ ይህ አላይ እንደ ማሳያ የተጠቀሰው እውነታ የሚያመለክተው እኒህ የሌብነት መረብ የዘረጉ  መኮንኖች በጥቅማቸው የመጣ ማንንም (የራሳቸውን) ሰው እንኳ ቢሆን እንደ ማይምሩ ይጠቁማል፡፡
በቃሊቲ እስር ቤት ከሚገኙ ዞኖች ዞን 6 እየተባለ የሚጠራው ገቢ በተለምዶ ሰሙ የዱርዬ ዞን በመባል ይታወቃል፡፡ እስር ቤቱ እንዲህ ብሎ ይሰየም እንጂ እዚያ ዞን የሚገባው ሁሉ ዱርዬ ነው ማለት 
 ከኢንጂባራው ዘላለም
አይደለም፡፡ ከሌሎች ዞኖች ጋር  በአንፃራዊነት ሲታይ ግን ወጣት የሚበዛበት ገቢ ነው፡፡ ይህ በመሆኑም በዞኑ አስተዳደሮች ጥሩ የገቢ ምንጭ በመሆን እያገለገለ ይገኛል፡፡  ከሚጨስ ሲጋራ ጀምሮ በክርንና በአፍንጫ እስከ ሚወስድ አደንዛዥ እፅ ድረስ እያስገቡ ይሸጣሉ፡፡ ይህ ደግሞ የሚፈፀመው ከዞን ኃላፊ መኮንኖች ጋር በሚሰሩ መኖርያቸውን በዚሁ ላደረጉ ተመላላሽ እስረኞች አማካይነት ነው፡፡ ጫትና መጠጥ ገንዘብ ላለው ሰው በቀላሉ ይቀርቡበታል፡፡


ይህንን ህገ ወጥ ስራ ለመስራት ቅድሚያ ለትግርኛ ተናጋሪ የሚለው ህግ ሳይፃፍ የተደነገገ ሳይታወጅ በሁሉም አይምሮ የፀደቀ በመሆኑ ተግባራዊ ይደረጋል፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ ቃሊቲ ዞን ሁለትም ከላይ የተጠቀሱት ነገሮች በሙሉ ይከናወናሉ፡፡ ይህ ማለት በሌሎች ዞኖች የለም ማለት ሳይሆን እነዚህ ሁለት ዞኖች ለማሳያ ያህል የቀረቡ መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ማንኛውም ይህን እውነት ማጣራት የሚፈልግ አካል በራሱ መንገድ ማጣራትም ሆነ ማጥናት ይችላል፡፡
በአጠቃላይ የሥርዓቱ ሎሌ የሆኑ መኮንኖች የሚፈፀሙት በደል ግፍና ቅሌት ይህ ተብሎ የማያልቅ ሲሆን የስርዓቱና የስረዓቱ ተከታዮች የስብእና መለኪያ ተደርጐ ሊወሰድ ይችላል፡፡ በሚቀጥለው ፅሁፌ የተደራጁ ወንጀለኞች ምሽጋቸውን በእስር ቤት አድርገው ከተማው ውስጥ እንዴት  ማጭበርበር እንደሚፈፅሙ የእስር ቤት አዛዦች በዚህ ላይ ያላቸው ሚናና ተሳትፎ እንዲሁ በአንድ የሃገሪቱ ቱጃር ገንዘብ እየተከፈላቸው ስለሚያሰቃዩት ግለሰብ ታሪክ ይዤ እቀርባለሁ እስከዚያው ቸር እንሰንብት!!

No comments:

Post a Comment