Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Saturday, August 18, 2012

የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንትን ለመምረጥ ፍትጊያው ቀጥሎአል

ኢሳት ዜና:- ነሀሴ ፲፪ (አስራ ሁለት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም
ከምግብ መመረዝ ጋር ተያይዞ በከፍተኛ ሕመም ምክንያት ከኃላፊነታቸው ለመነሳት ከአንድ ዓመት በፊት የስራ መልቀቂያ ጥያቄ ያቀረቡት የኦህዴድ እና የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት እንዲሁም የኢህአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል የሆኑት አቶ አለማየሁ አቶምሳ እስካሁን ጥያቄያቸው ምላሸ ባለማግኘቱ ፣ እርሳቸውን ማን ይተካ የሚለው ጥያቄ በኦህዴድ ውስጥ ከፍተኛ ውዝግብ መፍጠሩ ታውቋል።

በጳጉሜ ወር 2002 ዓ.ም በአዳማ በተካሄደው የኦህዴድ 6ኛ ድርጅታዊ ጉባዔ ተመርጠው የፓርቲውን የሊቀመንበርነት ሥልጣን ከአቶ አባዱላ ገመዳ የተረከቡት አቶ አለማየሁ ብዙም ሳይቆዩ በመስከረም ወር 2003 ዓ.ም የክልሉ ፕሬዚዳንት ሆነው ተሹመዋል፡፡


በአሁኑ ወቅት የ44 ዓመት ጎልማሳ የሆኑት አቶ አለማየሁ የፓርቲውንና የክልሉን ሥልጣን ሲረከቡ በክልሉ አይን ባወጣ መንገድ የሚካሄደውንና በአቶ አባዱላ ዘመን ስር የሰደደውን ሙስና መታገል የመጀመሪያ ሥራቸው እንደነበረ፣ ከዚሁ ጋር ተያይዞ አካሄዳቸው ባልጣማቸው ጓዶቻቸው ዘንድ በክፉ አይን መታየት መጀመራቸውን ምንጮችን ዋቢ በማድረግ የኦሮሚያ ክልል ዘጋቢያችን ገልጧል።
ፕሬዚዳንቱም ባልታወቀ ሁኔታ ብዙም በሥራ ላይ ሳይቆዩ መታመማቸውና ሕመማቸውም ከምግብ መመረዝ ጋር መያያዙ የቅርብ የስራ ባልደረቦቻቸው መድሃኒት ሳያበሉዋቸው እንዳልቀረ ጥርጣሬ ማሳደሩ ታውቆአል፡፡
ባለፈው ዓመት ነሐሴ ወር ለአራት ወራት በታይላንድ ሕክምናቸውን ሲከታተሉ ቆይተው ወደ አገር ቤት የተመለሱ ቢሆንም የጤናቸው ሁኔታ ግን ሙሉ በሙሉ ሊስተካከል እንዳልቻለ ታውቆአል፡፡አቶ አለማየሁ ከአንድም ሁለት ጊዜያት ያህል የሥራ መልቀቂያ ጥያቄ ለአቶ መለስ ዜናዊና ለፓርቲው ያቀረቡ ቢሆንም እሳቸውን የሚተካ ሁነኛ ሰው በማቅረብ ረገድ ፓርቲው በመቸገሩ ጥያቄያቸው ምላሸ ሳያገኝ መቆየቱን ምንጫችን አስታውሶአል፡፡

ክልሉ በአሁኑ ወቅት በምክትል ፕሬዚዳንቱ በአቶ አብዱልአዚዝ መሐመድ የሚመራ ሲሆን አቶ አለማየሁ ከጤና ችግራቸው ጋር በተያያዘ መደበኛ ሥራቸውን በመሥራት ላይ ባለመሆናቸው ፓርቲው በምትካቸው ሌላ ሰው ለመምረጥ ስብሰባ ተቀምጧል። አቶ አባዱላ ገመዳ የክልሉን ፕሬዚዳንትነት ስልጣን መልሰው ለመያስ ጥረት እያደረጉ ቢሆንም ከሌሎች አባሎች ከፍተኛ ተቃውሞ ገጥሞአቸዋል።

አቶ አለማየሁ አቶምሳ ወደዚህ ከፍተኛ ኃላፊነት ከመምጣታቸው በፊት የክልሉ ማስታወቂያ ቢሮ ኃላፊ በመሆን በመስራት ላይ ነበሩ፡፡አቶ አለማየሁ በትምህርታቸው ከሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ በሕግ በዲግሪ፣ከቻይና በሕዝብ አስተዳደር ሁለተኛ ዲግሪያቸውን አግኝተዋል፡፡በ2002 ዓ.ም ምርጫ በምስራቅ ወለጋ ዞን በሶሬ ወረዳ ለክልሉ ም/ቤት ተመርጠዋል፡፡

የኦሮሚያ ክልልን ከ10 ዓመታት በላይ በፕሬዚዳንትነት ያገለገሉት አቶ ኩማ ደመቅሳ ሲሆኑ ከኢህአዴግ ተሃድሶ ወዲህ አቶ አባዱላ  የጄነራልነት ማዕረጋቸውን ትተው በሲቪል “አቶ” ተብለው የክልሉ ፕሬዚደንት ሁነው ከሰሩ በኃላ በአቶ አለማየሁ ተተክተዋል፡

ኦህዴድ በአሁኑ ወቅት በአ/አ ስታዲየም አካባቢ ከ70 ሚሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ ባስገነባው ዘመናዊ ሕንጻ ውስጥ ከ2.2 ሚሊየን በላይ አባላቱን እያስተዳደረ ይገኛል።

No comments:

Post a Comment