Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Tuesday, May 29, 2012

ኢትዮጵያ ውስጥ የስልክ እና የኢንተርኔት አገልግሎት በየጊዜው እየታወከ ነው

ኢሳት ዜና:-
ዘጋቢዎቻችን ተዘዋውረው ያነጋገሩዋቸው የአዲስ አበባና የክልል ነዋሪዎች እንደሚሉት ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የስልክና የኢንተርኔት አገልግሎት ፍጹ ም እየታወከ በመምጣቱ እርስበርሰም ሆነ በውጭ ካሉ ዘመዶቻቸው ጋር  መገናኘት አልቻሉም። በያዝነው ሳምንት የሞባይል አገልግሎት በተደጋጋሚ ሲቆራረጥ እንደ ነበር ነዋሪዎች ገልጠዋል። በተለይ ወጣቶች የኢንተርኔት አገልግሎት በየደቂቃው እየታወከባቸው በፌስቡክና በኢሜል ከጓደኞቻቸው ጋር መገናኘት አልቻሉም።

አንድ ስሙ እንዳይጠቀስ የፈለገ ጋዜጠኛ ” መንግስታችን የኢንተርኔት አገልግሎቱን እያወከ አስቸግሮናል፣ ተራ ብሎጎቻችን ሁሉ እየተዘጉብን ደንግጠናል።” ብሎአል። የአሁኑ ተደጋጋሚ የፌስ ቡክ እና የሞባይል መታወክ ከጋዜጠኛ አበበ ገላው አጋጣሚና እና  ከሙስሊሙ ተቃውሞ ጋር ሊያያዝ እንደሚችል ዘጋቢዎቻችን የጠየቁዋቸው አስተያየት ሰጪዎች ይገምታሉ።

መንግስት የአበበ ገላው ፍሪደም “ነጻነት” የሚለው ቃል በኢንተርኔት እንዳይሰራጭ ከፍተኛ ቁጥጥር ማድረጉ ይታወቃል። ሙስሊም ኢትዮጵያውያንም ለጁመአ ተቀውሞ መልእክቶችን በኤስ ኤም ኤስና በፌስ ቡክ መላላካቸው ገዢው ፓርቲ ተጨማሪ የማወክ ስራ እንዲሰራ ሳያደርገው አይቀርም። ካለፈው ሳምንት ጀምሮ የጋዜጠኛ አበበ ገላው ፍሪደም “ነጻነት” የሚለው ቃል በሞባይል ብሉቱዝ ሰዎች ከመቀባባል አልፈው አዟሪዎች በሲዲ አባዝተው እየሸጡት ነው።

መንግስት በአሁኑ ጊዜ ምንም አይነት የተቃውሞ ድምጾችን ለመስማት ትእግስቱ እንደሌለው የሚወስዳቸው እርምጃዎች እንደሚያመላክቱ ነዋሪዎች ይናገራሉ። ኢሳት ቀደም ብሎ በአረብ ሳት ስርጭት በጀመረ በወራት ውስጥ እንዲታፈን ሲደረግ፣ የኤርትራ ቴሌቪዥን ደግሞ አንዳንድ የኢሳት ዝግጅቶችን ከዩቱዩብ ላይ እየወሰደ ማስተላላፍ እንደጀመረ ገዢው ፓርቲ በተመሳሳይ ስራ የኤርትራ ቴሌቪዥን የአረብ ሳት ስርጭት እንዲቋረጥ አድርጓል። 

ይሁን እንጅ ገዢው ፓርቲ የራሱንም ጣቢያ አብሮ እንዲታወክ በማድረጉ በአሁኑ ጊዜ በአረብሳት ይተላለፍ የነበረው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ተቋርጧል። የውስጥ ምንጮች እንደሚናገሩት በኢትዮጵያ መንግስትና በአረብ ሳት ባለስልጣናት መካከል ከፍተኛ ቅራኔ እና ውዝግብ ተከስቷል።

በራስ መተማመን የጎደለው የሚመስለው የመለስ መንግስት፣ በአገር ውስጥ የሚታተሙ ጋዜጦችን ለማፈን በአታሚዎች በኩል ያወጣው ህግ ነጻ ሚዲያውን ያሳሰበ ጉዳይ መሆኑን በተደጋጋሚ መዘገባችን ይታወሳል።  በተመሳሳይ ዜና ማተሚያ ቤቶች የቅድመ ምርመራ ውል እንዲፈርሙ እየወተወቱ ያሉት የግሉ ፕሬስ ተቋማት በውስጣቸው ያለባቸውን ክፍተቶች ለመድፈን የሚረዳቸውን ሁለት ዓይነት አደረጃጀቶች ተግባራዊ ለማድረግ እየተንቀሳቀሱ ይገኛሉ። 

ምንጮቻችን እንደገለጹት አሳታሚዎቹ ለሚያጋጥሙዋቸው ችግሮች በጋራ ሆነው ድምጻቸውን ለማሰማት አለመቻላቸውን ግምት ውስጥ በማስገባት አንድ ጠንካራ ማህበር ለማቋቋም ከሰምምነት ላይ ደርሰዋል፡፡በተጨማሪም ከመንግስት ማተሚያ ቤቶች ጥገኝነት ለመላቀቅ “የኢትዮጵያ ሚዲያ ዴቨሎፕመንት አክስዮን ማህበር” የተሰኘ የንግድ ማህበር ለማቋቋም ተሰማምተው ወደ ምስረታ ሒደት ተሸጋግረዋል፡፡

አ/ማህበሩ 500ሺብር ካፒታል የሚኖረው ሲሆን የአንዱ አክስዮን ዋጋ አንድ ሺብር ሆኖ በ500 አክስዮኖች የተከፋፈለ ነው፡፡አክሰዮን ማህበሩ ማንኛውንም የሕትመት ሥራ ለማከናወን፣የዲጂታል ቱክኖሎጂ ሕትመት ኢንዱስትሪ ውስጥ ለማሰተዋወቅ፣ሚዲያ ነክ በሆኑ ሌሎች ሥራዎች ላይ መዋዕለ ንዋዩን ለማፍሰሰ የሚያልም ነው፡፡

ሌላኛው “የኢትዮጵያ ፕሬስ አሳታሚዎች ማህበር” የሚል ጊዜያዊ መጠሪያ የተሰጠው ማኀበር አባላቱ ጠንካራ አቋም በመያዝ በተደራጀ መልክ ችግሮቻቸውን ለመፍታትና ለኢንዱስትሪው ዕድገት የበኩሉን አስተዋጽኦ ለማድረግ ያለመ ነው፡፡

 አሳታሚዎቹ ከሳምንት በፊት የብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት ያቀረበውንና ቅድመ ምርመራን ያሰፍናል በሚል የተቃወሙትን ውል በተመለከተ አማራጭ ሃሳባቸውን ለማኔጅመንቱ ካቀረቡ በኃላ በጉዳዩ ላይ ተወያይተው የመጨረሻ ውሳኔ ላይ ለመድረስ የማተሚያ ቤቱ የሥራ ኃላፊዎች ጥሪ እንደሚያደርጉላቸው ገልጸው ከተሰናበቱ በኃላ መልሰው አልተገኛኙም፡፡

No comments:

Post a Comment