Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Wednesday, July 25, 2012

የድህረ መለስ ዜናዊ ኢህአዴግ ምን መልክ ይኖረው ይሆን?

መለስ ብቻቸውን ኢህአዴግ ናቸው!

የኢህአዴግ መስራች ከሆኑት ፓርቲዎች የበላይ የሆነው ህወሓት በተለይም በጣምራ አመራር (collective leadership) ይታወቅ ነበር፡፡ ከ1971 ዓ.ም በፊት ሁለት ደረጃዎች ለነበሩት የህወሓት አመራር ሁለተኛው ረድፍ ላይ ተቀምጠው የነበሩት መለስ ዜናዊ በዓመቱ በተካሄደው የድርጅቱ ኮንግረስ ወደ መጀመሪያው ረድፍ አመራር መጡ፡፡ 

ከዚያ ቀደም የመጀመሪ ረድፍ የነበሩት አባይ ፀሐዬ፣ ስብሃት ነጋ፣ አረጋዊ በርሄ፣ ግደይ ዘርዓ ፅዮንና ስዩም መስፍን ነበሩ፡፡ መለስ ዜናዊ ወደነኚህ የመጀመሪያ ደረጃ አመራር የመጡበት ምክንያት በወቅቱ ኮንፍረንስ የተወሰነው ሶሻሊስት ፓርቲ የመመስረት ዕቅድ ነበር፡፡ ማዕከላዊ ኮሚቴው ይህን የሶሻሊስት ፓርቲ እንዲመሩ የሰየማቸው አቶ መለስ ዜናዊ ውሳኔው የጦር ሜዳ ውሎ ቀንሶላቸዋል፡፡ ቀጥሎም የካድሬ ት/ቤት ዋነኛ ተዋናይ፣ አንባቢና የሀሳብ አመንጪ ሆኑ፡፡


በ1977 ዓ.ም ማሌሊትን ለምስረታ ሲያበቁ ከድርጅቱ ሊቀ መንበር አቶ ዓባይ ፀሀዬ ቀጥለው ሁለተኛውን ደረጃ ያዙ፡፡ ሌላው የመለስ ዜናዊን ደረጃ ከፍ ያደረገው በምስረታው ወቅት ከግዳይ ዘርዓ ፅዮን ጋር የአይዲዮሎጂ ግጭት መፍጠራቸው ነበር፡፡ በወቅቱ የድርጅቱ ሊቀ መንበር ድጋፍ የተቸራቸው መለስ ዜናዊ ግደይን ካስባረሩ በኋላ እየገነኑ ወጡ፡፡ በ1983 ዓ.ም የመንግስት ስልጣን ሲይዙ የአቶ መለስ አስፈላጊነትና ከጣምራ አመራር መጥቆ የመውጣት አዝማሚያ ታየ፡፡

 የፖለቲካ ተክለ ስብዕናቸውን ለመገንባት የተለያዩ ዘዴዎችን ሲጠቀሙ የነበሩት አቶ መለስ የመጨረሻዎቹን ቋጥኞች ስልጣን በጨበጡ በ10 ዓመታት ውስጥ ከረበቷቸው፡፡ በ1993 ዓ.ም ህወሓትን ለሁለት የሰነጠቀው የውስጥ ግጭት የመለስ ዜናዊ ተቀናቃኞችን ያለ ፖለቲካ ስልጣን በተናቸው፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ መለስ ዜናዊ ማለት ኢህአዴግ፣ ኢህአዴግ ማለት መለስ ዜናዊ ሆኑ፡፡
ባለፉት 20 ዓመታት ኢህአዴግን ሲከታተሉ እንደቆዩ የሚናገሩት ዶ/ር ሙሉ አበራ ‹‹መለስ ራሱ ስርዓት (system) ሆኗል፡፡ መለስ ችግር ሲገጥመው ስርዓቱን ችግር ይገጥመዋል›› ይላሉ፡፡ አርባ አመት ሙሉ ፖለቲካ ያስተማሩት ዶ/ሩ ‹‹መለስ ኢህአዴግን ሲሰራ ፖለቲከኛ እንዳይወጣ ተከላክሏል›› ሲሉ ይተቻሉ፡፡ በፓርቲው ውስጥ አንብበዋል የተባሉት እነ ተወልደ ወልደማርያም፣
አለምሰገድ ገብረአምላክ፣ አውአሎም ወልዱ፣ ገብሩ አስራት፣ አልተረፉም፡፡

በተቃራኒው አሁን ያሉትን እነ አለቃ ፀጋዬ በርሄ፣ አባይ ወልዱ፣ ደብረፅዮን ገብረሚካኤል፣ ቴዎድሮስ አድሃኖምን የመሳሰሉት የፖለቲካ ተክለ ቁመናቸው የወረደ እንደሆነ ይነገራል፡፡ ‹‹ኢህአዴግ ካድሬ ብቻ አለው›› የሚሉት አንድ አስተያየት ሰጪ ‹‹እነኚህ የተባለውን ብቻ የሚደግሙ እንጂ የሚፈጥሩም፣ የሚጠይቁም አይደሉም›› ይላሉ፡፡ በአስተያየት ሰጪው ትንተና ‹‹ሽመልስ ከማል፣ ሬድዋን ሁሴን፣ ተፈራ ደርበው፣ ቴዎድሮስ አድሃኖም›› በዚህ ምድብ ናቸው፡፡

በተለይ ህወሓት ተተኪ የሌለው መሆኑን አብዛኞቹ ሰዎች ይስማሙበታል፡፡ከላይ ከተጠቀሰው በተቃራኒ ኢህአዴግ የመተካካት ፖሊሲ በመንደፉ ምንም ችግርአይመጣበትም የሚሉ አስተያየት ሰጪዎች አሉ፡፡ መለስ ዜናዊ በተለይ በግንባሩ ሊከሰት የሚችለውን የስልጣን ሽኩቻ ለመቀነስ ም/ጠ/ሚኒስትሩን ከደቡብ መምረጣቸውን ዋቢ በማድረግ ይከራከራሉ፡፡

 ስሜ መጠቀስ የለበትም ያሉ አስተያየት ሰጪ በበኩላቸው ‹‹መለስ ከማንም በላይ በኤርትራዊ አጀንዳ መጠመዱን ህወሓት ባያውቅም ስልጣን እና ጠመንጃ በእጁ ነው፤ ኢኮኖሚውንም ወደ መቆጣጠሩ ገብቷል፤ ምንም ቢፈጠር ስልጣኑን በሆነ መንገድ ያለችግር ያስኬዳሉ›› ይላሉ፡፡ አስተያየት ሰጪው ጉዳዩን “in this line of reasoning ነው ማየት የሚቻለው›› ይላሉመቀሌ ዩኒቨርሲቲ የፍልስፍና መምህር የሆኑት አቶ መምሬ ውለታው (ስም የተቀየረ) ‹‹የድህረ መለስ ኢህአዴግ መልካም አጋጣሚ ይኖረዋል›› ይላሉ፡፡

 በመለስ ዙሪያ ያሉትን ሰዎች በመዘርዘር ምሳሌ የሚሰጡት አቶ መምሬ ኤርትራዊ የኋላ ታሪክ ያላቸውና በመለስ ዙሪያ ወሳኝ ሚና ያላቸውን ሰዎች በማባረር ኢትዮጵያዊነትን መላበሱን ይሞግታሉ፡፡ ‹‹ህጉን በማጠላለፍ እያወጣ የሚያሳስረው ፋሲል ናሆም ነው፤የም/ጠ/ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ኃ/ማሪያም ደሳለኝ ታኮ አምባሳደር ብርሃነ ገብረ ክርስቶስ ናቸው፤ የበሬ ወለደ መረጃ የሚያቀብለንና የቤተ መንግስት ሚዛን አስጠባቂ የሆነው ሰው አቶ በረከት ነው፡፡ 

ሳሞራ ወታደሩን ያዛል፤ ኪዳኔ፣ ኢሳያስ … የተባሉ ሰው የማያውቋቸው በያንዳንዱ ጀርባ ያሉ ኤርትራዊ ናቸው›› ይላሉ፡፡ይህን ትንታኔ የሚደግፉ አስተያየት ሰጪዎች የባድመ ጦርነት ወቅት ‹‹መለስ ዜናዊ ሰላማዊ መፍትሄ›› እያሉ የነበረው የጦርነቱ መንስዔ የሆነው የብዝበዛው ድርጊት እንዲቀጥል የተመቻቸ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ ኢትዮጵያዊነትን የሚያቀነቀኑ ቡድኖች ጦር ሜዳ ሲዋጉ እርሳቸው መፈንገያ የሚሆናቸውን ቦና ፓርቲዝም ይፅፉ እንደነበር ይነገራል፡፡ ባሸናፊነት የተደመደመውን ጦርነት አሰብ ድረስ በመሄድ የመደራደሪያ ካርድ እንዳይሆናቸው መከላከላቸውም ይነገራል፡፡ በመቀጠልም ‹‹በህግ ስም አስነጠቀን›› ይላሉ፡፡
                             ‹‹Business as usual››
የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህፓርቲ የህዝብ ግንኙነት የሆኑት ዶ/ር ኃይሉ አርዓ ‹‹መለስ ካድሬውን ከፋብሪካ እንደወጣ ምርት አንድ አድርጎ በመስራቱ ከህልፈታቸው በኋላ እንኳ ለውጥ እንዳይጠበቅ ማድረጉን ይናገራሉ፡፡ ‹‹ችግሩ ከካድሬው ጀምሮ ነው›› የሚሉት ዶ/ሩ ‹‹ጠ/ሚኒስትሩ ቢያልፉም እንኳ በመንፈስ በነርሱ ላይ ሰፍረው ይኖራሉ፤ የድርጅቱ ባህሪም ያው ነው፤ ባይሆን እኮ ከዚህ በፊት እርሳቸው እያሉም ፍንጭ ይታይ ነበር፤ መለስ እንዲህ አለ፤ እከሌ ደግሞ በተቃራኒው እንደዚያ አለ ተብሎ አያውቅም›› በማለት የተለየ ነገር ከኢህአዴግ እንደማይጠበቅ ይመክራሉ፡፡ 

ዶ/ር ኃይሉ ‹‹ሌላ ሰው ቢመጣ አንደኛ ሌላ ሰው በመሆኑ ሁለትም ከመጣበት ባህል አንፃር ትንሽ ልዩነት ቢኖረውም ስር ነቀል ለውጥ (fundamental change) የለም›› ሲሉ ይደመድማሉ፡፡ በአዋሳው 7ኛ ድርጅታዊ ጉባኤ ‹‹መተካካት›› የምል ሀሳብ በአዲስ ሁኔታ ቢታይም ተግባሩ አሮጌ ጠጅ በአዲስ አቁማዳ ነው›› ይላሉ፡፡በመተካካት ዙሪያ ብዙ ቢባልም ከተመረጡት 36 ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት አዲስ ስም ሆኖ የተካተተው 6 ብቻ ነበሩ፡፡ ይህ ከመቶኛ ሲሰላ 16.6 ነው፤ በሁለት ዙር ሙሉ በሙሉ አዲስ አመራር ለመገንባት የፈለገ ፓርቲ 83.4 በመቶ ባንዴ ለመተካት ቢሞክር አደጋው የሚከፋ ይሆናል፡፡
ቻይናኛፖለቲካ

ኢህአዴግ ከያንዳንዱ አባል ደርጅት የተውጣጡ 180 የም/ቤት አባላት ያሉት ሲሆን ከያንዳንዱ የግንባሩ ፓርቲ 45 ሰዎች ይወከላሉ፡፡ ከነዚህ የምክር ቤት አባላት ሌሎች አስራ አምስት ሰዎች ከያንዳንዱ ፓርቲ ተመርጠው 45 ሰዎች የማዕከላዊ ኮሚቴ ይሆናሉ፡፡ የግንባሩ አባላት 9 ሰዎችን ለስራ አስፈፃሚነት የሚመርጡ ሲሆን ፖለቲካውን የሚዘውረው ይህ ስራ አስፈፃሚ ነው፡፡ እንደ ፖለቲካ ተንታኞች አባባል የኢህአደግ ስራ አስፈፃሚ ከቻይናው ፖሊሲ ቢሮ ጋር እኩል ነው፡፡ 

የፍልስፍና መምህሩ ከዚህ በታች ያለውን የትኛውም አመራር ‹‹ፖለቲካዊ ውሳኔ ላይ ምንም መብት ስለሌለው ድህረ መለስ mኢህአዴግ ላይ የሚፈጥረው ለውጥ ትርጉም አልባ ነው›› ይላሉ፡፡ ስራ አስፈፃሚው የፖሊሲ ክለሳና ለውጥ ብቻ ሳይሆን የስልጣን ሽግሽግም በመምራቱ ‹‹የኢህአዴግ ፖለቲካ ቻይንኛ ነው›› ይላሉ መምህሩ፡፡ አስተያታቸውን ለፍኖተ ነጻነት የሰጡት እኚህ መምህር አቶ በረከት ስለ ጠ/ሚኒስትሩ ጤና ለህዝብ ይፋ ያለማድረጋቸውን ሲጠየቁ የመለሱት መልስ ብቻ ሳይሆን አመላለሳቸውም ‹‹ጥብቅ ማዕከላዊነትን ያመላከተ ነው›› ይላሉ፡፡

ትልቁ ሽንቁር 
ኢህአዴግ መሬት ላይ ካለው ጥንካሬው ይልቅ የሚያስተጋባው (echo) ይበልጣል፡፡ ብሔር ላይ ያለቅጥ መመስረቱን እስካልቀየረ ድረስ ህብረ ብሔር መሆን እንደሚከብደው የሚደመድሙ አልጠፉም፡፡ ፓርቲው እስከ ቀበሌ ድረስ በመውረድ ጠንካራ መዋቅር መዘርጋቱ ፓርቲውን የማይነቃነቅ አስመስሎታል፡፡ አቶ መለስ ዜናዊ በህይወት ከቆዩ ስልጣን ቢለቁ እንኳ ከኋላ በመሆን ሁሉን ለመከወን መዘጋጀታቸውን (Putinism) በተለያዩ ወቅቶች ድህረ ስልጣን በምን ሁኔታ እንደሚቆዩ ለተጠየቁት ጥያቄ ከሰጧቸው መልስ መረዳት እንደሚቻል የፖለቲካ ታዛቢዎች ይናገራሉ፡፡ ከዚህ በተቃራኒ ፖለቲካው ባለበት በድንገት ጥለው የሚያልፉ ከሆነ የፖርቲ ውስጥ አንድነት (Harmony) ያለመገንምባት የርስ በርስ ሽኩቻ ማስከተሉ አይቀሬ መሆኑን ታዛቢዎቹ ያስቀምጣሉ፡፡ 

በተጨማሪም ተቃዋሚዎች፣ የራሱ የኢህአዴግ አኩራፊዎች፣ ነፍጥ አንጋቾችና መንግስት አልባነት የሚጠቀሙበት ቡድኖች የኢህአዴግ ፈተና ሊሆኑ እንደሚችሉ ይነገራል፡፡ በነዚህ ሁኔታዎች ገና ያልተፈተነውን ኢህአዴግ ‹‹ጠንካራ የሚመስል ግን ልል›› /Brittle but stable/ ስሉ ይገልፁታል፡፡

 ሽኩቻው ላይ ማን ይሳተፋል? 

ዶ/ር ሙሉ አበራ ‹‹አማሮቹ የኢትዮጵያን መዳን ይፈልጋሉ›› ሲሉ ይጀምራሉ፡፡ ‹‹የበላይነት በጭራሽ አይፈልጉም፤ ይልቅ በአማራ ስም የተወከለውን የፊውዳል ስርዓት የተዋጋው ማን ነው? ኢህአፓ ውስጥ ስንት የፊውዳሉ ልጆች ስርዓቱን የሚገነድስ ‹መሬት ለአራሹ›ን አቀንቅነዋል? መኢሶን ውስጥስ? አማራ የህይወት መስዋዕትነት ከፍሏል፤ ትግሬኛ ተናጋሪዎቹ ከነቁ ከሻዕቢያ መንፈስ ተላቀው ከአማሪኛ ተናጋሪው ጋር ቢወግን የወጣዋል፡፡ 245 ነገስታት ከጥንት እስከ ቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ ድረስ የነገሱ ሲሆን አብዛኛው ከሰሜኑ አከባቢ ነበሩ›› ይላሉ፡፡ ዶ/ር አማርኛ ተናጋሪው ‹‹ይልቅ ኢትዮጵያን ለማዳ ሽኩቻ ውስጥ ሳይገቡ አይቀርም›› ይላሉ፡፡

መምሬ ውለታው በበኩላቸው ‹‹ኃ/ማሪያም ለስልጣን ሩቅ ነው፤ ቀጣዩን መምረጥ የቅራኔ ምንጭ ሊሆን ይችላል፤ ኢህአዴ ‹harmony› የሌለው ቡድን ነው›› ካሉ በኋላ ምክንያታቸውን ሲያስቀምጡ ‹‹ከንግዲህ መለስ የገነቡትን በማስፈራራት ውሳኔ እንዲቀበሉ የማድረግ ሂደት ከንግዲህ ለመኖራቸው ይፈቱታል፡፡›› በተለይ ኦሮሞና አማራ ብሔርን እንወክለዋለን የሚሉት ሁለቱ ገዢ ፓርቲዎች አሁን የቁጥራቸውን ያክል የስልጣን ድርሻ እንደሚፈልጉ የገልጻሉ፡፡

ይህ ፌደራሊዝሙ የተሰራበትን ነጥብ የያዘ ነው፤ከንግዲህ ህወሓት ወደስልጣን ከመጣ ሌላውን ያስኮርፋል፣ የአማራዎቹ መምጣትም “ነፍጠኞችን እንዋጋ” ከሚለው የህወሓትና ኦህዴድ መፈክር አንፃር ከባድ ሊሆን እንደሚችል ይነገራል፡፡ ያም ሆነ ይህ ከኦህዴድና ከብአዴን የአንዳቸው ወደ ግንባር መምጣት አናሳዎቹን የመዋጥ ዕድል እንዳለው ስለሚተነተን ህወሓት አጋር ቡድኖቹንም
ከጎኑ የማድረግ አቅም አለው ተባሉ ይገመታል፡፡

 በቅርብ ጊዜ ከፍተኛ ኃላፊነት የያዙት የኢህዴን ሰዎች ከ40 በላይ ብሔረሰቦችን የወከሉ ናቸው፡፡ ‹‹ኦህዴድ ለመሬት ቅርምት እና ለህወሓት እጅ አዙር አገዛዝሽፋን የቆመ ነው፡፡ እነ አባ ዱላ ሞራል ኖሯቸው ለስልጣን አይቀናቀኑም›› ይላሉ ዶ/ር ሙሉ፡፡ኢህአዴግ የቀድሞውን ያክል አይሆንም በመለስ መታመም /መሞት የተነሳ ‹‹ከርሳቸው ውጭ ሰው የለም የሚሉት አባላት በድርጅቱ ላይ እምነት እንደሚያጡ ይነገራል፡፡

 በተጨማሪም ተተኪ የሚሆኑ ሰዎች በአግባብ የተለዩ  ከመሆናቸውም በላይ አቋማቸው በተግባር አልተፈተሸም፡፡ ሌላው መንገድ በህይወት ተርፈው ግን መስራት የማይችሉበት ሁኔታ (incapacitate) ከተፈጠረም ያው መሆኑ ይገመታል፡፡ ቀጣዩ ጠ/ሚኒስትርም የመለስ አይነት ስብዕና ለመገንባት አሁን ያለው የመለስ ድባብ (posthumous) እንኳ ጥላ ያጠላበታል፡፡ በግለሰብ ደረጃም ቅራኔ ሊገጥመው ይችላል፡፡ ዶ/ር ሙሉ ‹‹መለስን ጨምሮ በፖለቲካ ሴራ የተካኑት አንጋፋዎቹ እያለፉ በመሆኑ አቶ በረከት ሰሞኑን እንዳሉት ፓርቲው ውስጣዊ ችግሮቹን እንደከዚህ ቀደሙ እዚያው ይዞ መፍታቱ ያበቃበት ዘመን ነው›› በማለት ይደመድማሉ፡፡

No comments:

Post a Comment