Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Sunday, July 15, 2012

የኢህአዴግ ጥንካሬ ምን ያክል ነው?

እንቁላል በጫፍና ጫፉ በመዳፍ መሃል አይሰበርም
ሙላቱ አርጋው ከመገናኛ ወደ ስድስት ኪሎ ሲነዱ በርጋታ ነው፤ የኢትዮጵያን ፖለቲካ፤ ኢኮኖሚና ስነ ልቦና ላለፉት 40 ዓመታት ስራዬ ብለው አንብበዋል፤ ባለፉት 21 ዓመታት የኢህአዴግን አስተዳደር እግር በግር ተከታትለዋል፤ “ኢህአዴግ ከተቃዋሚዎች አንጻር እጅግ ጠንካራ ነው፤ ጥንካሬው ግን በትክክለኛው መሰረት ላይ አይደለም’’ ይላሉ፡፡

 “ከመገናኛ ወደ ስድስት ኪሎ ስነዳ ቀጥ ያለው መንገድ የደህንነት ስሜት ይሰጠኛል፤ ጠንካራ የሚመስለው ግን ግዝፈቱ ወደ አንድ አቅጣጫ ያደላ የሚመስለው ኢህአዴግ ግን ያሳስበኛል፡፡” ይላሉ::

አብዮት ይከሰታል ?
 ስማቸውን ያልጠቀሱ ፀሐፊ የኢንተርኔት ሰፈር ላይ በጫኑት ዳሰሳቸው “በቱኒዚያ፤ ግብፅና ኢትዮጵያ መካከል ያለው አንድነት ምን እንደሆነ ሳስብ እንደ ቤን አሊና ሙባረክ ሁሉ አቶ መለስም ለአስርታት መሪነት ላይ ቆይተዋል፤ ኢትዮጵያ የአንድ ፓርቲ ስርዓት ሀገር ሆናለች፤ ሀሳብን በነጻነት መግለፁ (ኢንተርኔት፤ ህትመት ሚዲያው) የቅድመ ምርመራ ስራ ተጀምሮበታል፡፡ 

አስር ዓመታት ብቻ ከ70 በላይ ጋዜጠኞች ሀገር ጥለው ለመሰደድ ተገደዋል፤” እነኝህና ሌሎች መንስኤዎች ለአረቡ አለም ዓይነት አብዮት በቂ መነሻ ይሆናሉ ሲሉ ይከራከራሉ፡፡ በሌላ በኩል ጂፈሪ ቶሞሰን የተባሉ የፖለቲካ ተንታኝ ይህንን አተያይ ያጣጥላሉ፤ እንደ ቶሞሰን እይታ የአብየቱ መንገድ ጠራጊ ለሚሆን እንቅስቃሴ እንደ መሐመድ አልባራዲ፣ አሊያም ሙስሊም ወንድማማቾች አይነቶቹ የሉም፤ የቀድሞዋ ዳኛ ብርቱካን ሚደቅሳና በችሎቷ የቀረበው የቀድሞ መከላከያ ሚኒስትር ስየ አብረሃ ምን ይፈጥራሉ? ደግሞም በቦታው የሉም” ሲሉ ያለውን የአመቻት አካል እጦት ይገልጻሉ፡፡

 “Policy and political challenge” የሚል ሰነድ እንዳብራራው የኢህአዴግ ጠላት ራሱ ነው፤ ኢህአዴግ ለመግዛት የተዘጋጀ ቡድን ራሱ ብቻ እንደሆነ በማሰብ ሌሎችን ከመጠን ያለፈ ማናናቅ ስራው ማድረጉን ይናገራሉ፤ “ፓርቲው ሁለት ነገር ይዟል፤ ከፍተኛ የሰውና የገንዘብ ኃይልና ያልተሳካ ግን የረጅም ዘመን ስልጣን፤ ለረጅም ጊዜ በመግዛቱ የተነሳ ያተረፈው የህዝብ ጥላቻ፤ የሚያናንቃቸው ተፎካካሪ ቡድኖች ግን ትንሽ የሰው ኃይል እና ትንሽ ገንዘብ በጣም ከፍተኛ ከሆነ የህዝብ ኢህአዴግን ያለመፈለግ ንፋስ ይዘዋል” የሚለው ሰነዱ “ህዝቡ ኢህአዴግ ይወድቃል አይወድቅም ላይ ሳይሆን እንደ አህአዴግ ግዙፍ ድርጅቶች ሲወድቁ የሚከሰተውን ቀውስ” ለመድፈን ማሰብ መሆኑን ይተነትናል፡፡

 “ለራስ ሲቆርሱ …” ኢህአዴግ
አቶ መለስ ዜናዊ መንግስታቸው ለሚታማበትተፎካካሪዎችን የማሰር ተግባር አንድም ቀን ‘ተሸንፈው’ አያውቁም፤ የሚካሄዱ “እስሮች” ሁሉ መንግስታቸው በኢትዮጵያ ውስጥ ‘ለመጀመሪያ’ ጊዜ ለዘረጋው ህገ-መንግስታዊነት ጥብቃና መቆሙ አንደ ሆነ ሳይሰለቹ ያስረዳሉ፤ በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ የፖለቲካ ፓርቲ ሊቀመንበር የነበሩትን የወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳ እስር በተመለከተም በወቅቱ ለፓርላማ በሰጡት ማብራሪያ መንግስታቸው ለህግ የበላይነት ሲል ያሰራቸው በመሆኑ ‹‹ውሳኔው ያልጣመው በሊማሊሞ ማቋረጥ” ይቀለዋል እንጂ ለድርድር እንደማይቀመጡ አስረዱ፡፡

ፓላንዳዊ የመንግስታት ዴሞክራሲያዊ ባህሪያት አጥኚ የሆኑት Wiktor Osiatynski በዚህ አይስማሙም፡፡ “Constitution of principle Vs Constitution of Compromise” በተባለ የጥናት ሰነዳቸው ዴሞክራሲያዊ ያልሆነ ህገ-መንግስታዊነትን በሁለት መልኩ እንደሚያቀነቅኑ ያትታሉ፡፡ እነዚህ መንግስታት ህገ-መንግስታዊነትን ለራሳቸው ጥቅም ሲሆን አያስታውሱትም፤ ተቀናቃኞቻቸውን ለማጥቃት ሲሆን ግን የትኛውም እርምጃ ህገ-መንግስቱን የሚያፈርስ ናዳ አድርገው በማቅረብ ያስሯቸዋል፤ አሊያም መብታቸው እንዳልሆነ ይነግሯቸዋል ፡፡ 

በወጣቶች አደረጃጀት ከፍተኛ ደረጃ ደርሶ የነበረ አንድ ወጣት ኢህአዴግ በነበረባቸው ጊዜያትና አሁን ድርጅቱን በለቀቀበት መካከል ያለውን የመንቀሳቀስ መብት እንዲህ ያወዳድራል፤ “ ከዚህ በፊት ወጣት ሊግ ሆነ ወጣት ፎረም ውስጥ እያለን ለስብሰባ ፈቃድ ጠይቀን አናውቅም፤ ፍቃድ ጠይቁ ብሎ የጠየቀን አካል የለም” ሲል ኢህአዴግ በነበረባቸው ጊዜያት ‹ያልታሰበውን› ህገ-መንግስታዊነት ያስታውሳል፡፡

 ወጣቱ ድርጅቱን በአካሄድ ባለመስማማት ለቆ ከወጣ በኋላ ያቋቋሙት የወጣቶች ነጻና ገለልተኛ ማህበር ከማህበራት ማደራጃ ህጋዊ እውቅና ያለው ቢሆንም ፖሊስ ስብሰባ ማድረግ እንዳማይችሉ የከለከላቸው ዕለት “ለመሰብሰብ ፍቃድ የላችሁም ተብለን እንድንበተን ሲደረግ እና ከነበርንበት አዳራሽ በቅርብ ርቀት ህጋዊ ሰውነት የሌለው የወጣት ፎረም ከየትኛውም አካል ፍቃድ ሳይጠይቅ ስብሰባውን ያካሄድ ነበር” ሲል Osiatynski ሀሳብ የሚያጠናክር ምሳሌ ይሰጣል፡፡
የስልጣን ኢ-ተቋማዊነት
የኢህአዴግ ደጋፊዎች በመለስ ዜናዊ የመድረክ ጌታነት ይኮራሉ፤ በየአለም አቀፍ መድረኮች ብቻቸውን እየዞሩ በሚያሰሙት ዲስኩርም እንዲሁ ይደሰታሉ፡፡ ባለፉት 21 ዓመታት መንግስትን፣ ኢህአዴግንና ህወሓትን ያለማንም ጣልቃገብነት የመሩት አቶ መለስ ዜናዊ ተተኪ ባለማፍራት ግን በፖለቲካ አዋቂዎች ዘንድ በጅጉ ይኮነናሉ፡፡ መለስ ዜናዊን ለረዥም ጊዜ የሚተካውን ሰው በመምረጡ ረገድ ኢህአዴግን ለውጥረት እንዲሁም የመከፋፈል አደጋ ያደርሰዋል የሚሉ አሉ፡፡ የነዚህ ቡድኖች የመከራከሪያ ነጥብ ፓርቲው ብሔርን መሠረት ባደረጉ የኢህአዴግ ፓርቲ አባላት ዘንድ ለውጥረትም፣መቃቃር መፍጠሩም አይቀሬ ይሆናል፡፡

 በተለይ መረጋጋት በማይነበብባቸው ክልሎች መካከል መገፋፋት ሳይፈጥር አይቀርም፡፡ በተመሳሳይ መልኩ አቶ መለስ ዜናዊ ለረዥም ዘመናት የያዙት በትረ ስልጣን ተተኪ መሪ የሚሆኑ ወጣት ፖለቲከኞችን ያለ ማፍራቱ በኢትዮጵያ ዛሬም ስልጣን ተቋማዊ እንዳልሆነ መቅረቱን ያሳይል፡፡

መድሐኒቶች መርዝ ናቸው
እንደ ኢህአዴግ ዓይነት ዴሞክራሲያዊ ጉዳዮች ይመለከቱናል የሚሉ መንግስታት ለፖለቲካ ተቃውሞ ያላቸው ግብረ መልስ ጥንቃቄ ይጠይቃል፤ በኢትዮጵያ ነፍጥ ያነሱ በርካታ የመንግስት ተቃዋሚዎች አሉ፤ ሰላማዊ ትግልን በቀኖናነት የያዙ ቡድኖችን የሚገፋ የፖለቲካ ከባቢ ግን የፖለቲካ መፍትሄ ሳይሆን የመጥፎ ምልክት ነው፤ ቴዎድሮስ ካሳ የተባሉ ሰው “ኢህአዴግ በዚህ በኩል የወሰደው መድኃኒት መርዝ ሆኖበታል” ይላሉ፡፡ ቴዎድሮስ ዋነኛ ምሳሌ በማድረግ የሚያነሱት በኢትዮጵያ የፖለቲካ ፉክክር የኢኮኖሚ ትንተና የፖለቲካ ማዕከል እንዲሆን አድርገዋል በማለት የሚያነሷቸው ዶ/ር ብርሃኑ ነጋን ነው፡፡

የኢህአዴግ የፖሊሲ ማዕከል ድህነትን በመዋጋት ላይ ያተኮረ እንደሆነ ይናገራል፤ “policy & political challenge” የተባለው ሰነድ በበኩሉ ሁሉም እድገት ድሃውን ይጠቅማል ተብሎ ስለማይታሰብ ቁም ነገሩ ፍትሃዊ ዕድገትእንዲያጡ ያደርጋል፤ በሌላ በኩል ከብሔር ብሔረሰቦች፣ የሃይማኖት ነፃነት ችግርና የመሬት ጉዳይ ጀምሮ ኢህአዴግ ለፖለቲካ ትርፍ ሲል ጠርዝ ድረስ የወሰዳቸው እርምጃዎች መርዝ እንደሆኑበት ይተነትናል፡፡

በሐምሌ 2007 እ.ኤ.አ. የአሜሪካ ትልቁ የህዝብ አስተያየት ድምፅ ሰብሳቢ የሆነው ለጋሽ ድርጅት ከ15 ዓመት ዕድሜ በላይ ያሉትን 1000 ኢትዮጵያውያን ከጾታ፣ ቋንቋ ፣ክልል እና ሀይማኖት አንጻር ተመጣጣኝ ውክልና በመውሰድ ጥናት አድርጎ ነበር፡፡ ውጤቱን የተመለከተ አንድ ህትመት “ከሀይማኖት ድርጅት ሌላ ከግማሽ በላይ ቁጥር ያለው ኢትዮጵያዊ የሚተማመንበት አንድም የፖለቲካ ይሁን ማህበራዊ ተቋም የለም” ሲል ደምድሞ ነበር፤ የኢትዮጵያ ነክ ትንታኝ ምሁራንም የየራሳቸውን አስተያየት ሰጥተው ነበር፤ ኢትዮጵያ ላይ ሰፊ ምርምር በማድረግ የሚታወቁት የጆርጅ ሜሰን ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህሩ ቴሬንስ ልዮንስ “ሕዝቡ ለገዥው ፓርቲ ራሱን አስገዝቶ ሊሆን ይችላል፤ ይህ ማለት ግን በመንግስት ፖሊሲዎች ይስማማል ማለት አይደለም” ይላሉ፡፡

ፕሮፌሰሩ ጋሉኘ በሰራው ጥናት መሠረት ከአራት ኢትዮጵያውያን መካከል ሦስቱ የአገራቸው ፍርድ ቤቶች የተቋቋሙላትን ፍትህን የመወሰን እና ህግን በአግባቡ የመተርጎም ሚና ይወጣሉ ብለው እንደማያምኑ ተነግረዋል፡፡ በሪፖርቱ ተቃሞቻቸውን ባለማመን ኢትዮጵያውያን አፍሪካን የሚመሩ ነበሩ፡፡ መምህሩ ይህ “የአገሪቱ መረጋጋት በቋፍ ላይ እንዳለ ያሳያል” ይላሉ፡፡ በ2004 ዓ.ም ይፋ የተደረገ ሌላው የህዝብ አስተያየት ስብስብ በተመድ እና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ትብብር ተሰርቶ ነበር፡፡ ክሊማንጃሮ ኢንተርናሽናል ሊ.ቲ.ድ የተባለ የታንዛኒያ ድርጅት የሰራው ይህ ጥናት በድጋሚ ዋነኛ የመንግስት ተቋማት በዜጎቻቸው ካለመታመንም በላይ የጥርጣሬ ምንጭ እንደሆኑ አረጋግጧል፡፡

 ፍ/ቤቶችን ጨምሮ ዝቅተኛ ውጤት የተገኘበት ይህ ጥናት በሰኔ ወር ከተሰጠው ‹የአሸባሪዎችና ተባባሪዎቻቸው› የጥፋተኝነት ውሳኔ በፊት መሆኑ ደግሞ ነገሩን የበለጠ አሳሳቢ ያደርገዋል፡፡ ፕሮፌሰሩ “አትጠራጠሩ፤ ዜጋው የሚወደው ተቋም ከሌላው የሚወደው መንግስት አይኖረውም፤ አንዱ የኢህአዴግ የውድቀት መንስኤም፣ ያለ መረጋጋት ቢፈጠር፣ ዜጋው እንዳይጎዳ የሚቆምለት ነፃና ተዓማኒ ተቋም ካለመኖሩ የተነሳ አመፅ ቢነሳ እንዲያውም ተባባሪ ይሆናል” ሲሉ ይደመድማሉ፡፡

አቶ መለስ ሁሉም ነገር ለህግ-የበላይነት የቆመ ነው ቢሉም የቀድሞ የትግል ጓድና የመከላከያ ሚኒስትር የነበሩት ስየ አብርሃ ስለታሰሩበት ክስ የሚተነትን በጻፉት መፅሐፍ ሁሉም ነገር የግል ስልጣን የማስጠበቅ ፍላጎት እንደሆነ ያስረዳሉ፡፡ ይህን “ለራስ ሲቆርሱ አያሳንሱ” አካሄድ የሚተቹት አቶዊ ሚሊያም የተባሉ ሰው “ተርበው ሊበሉን የሚችሉ ሰዎችን ፊት በቁንጣን ተወጥረን መቅረብ ይመስላል” ሲል ይገልፁታል፡፡

ምን ይደረግ?
መሆኑን ያወሳል፡፡ እንደ ሰነዱ ትንተና ከሆነ እድገቱ ከህዝብ ብዛት ጋር መመጣጠን አለበት፤ 70 በመቶ የከተማ ወጣት ስራአጥ በሆነበት ሁኔታ ሀሳብን በነፃነት መግለጽ ያለመቻል ሲደመር ለመቃወም ዝግጁ ይሆናል፡፡ የኑሮ ደረጃ መራራቅ ድሆች በመንግስት ላይ እምነት አፍሪኮም (AFRICOM) የተባለው የአሜሪካ የአፍሪካ ኮማንድ መሰረቱን ዋሽንግተን ካደረገው አለም አቀፍ የስትራቴጂ ጥናት ማዕከል የሐሳብ አመንጪ ቡድን ጋር ባደረገው የጥናት ውል በቀጣዮቹ 10 ዓመታት ውስጥ ከፍተኛ ያለመረጋጋት የሚገጥማቸውን የአፍሪካ አገራት ለይቷል፤ በዚህ ያለመረጋጋት ቡድን ውስጥ አንዷ የሆነችው ኢትዮጵያ በተለይ የአረቡ ዓለም መነቃቃትን ተከትሎ ልከሰት የሚችለውን አለመረጋጋት ለመድፈን አሜሪካውያን ፖሊስ አውጪዎች የመጠባበቂያ ፕላን እንዲያዘጋጁላት አስገድዷቸዋል፡፡

የጥናቱ ዋና አላማ በቀጣዮቹ አለመረጋጋት ይታይባቸዋል የተባለው እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ሀገራት የሚነሱ ቀውሶችን በወታደራዊ ኃይል የመፍታት ቅድሚያ ስለሚወስዱ እና ይህንን የሚያስቀር መንገድ መቀየስ ላይ የተኮረ ነው፡፡ በአጠቃላይ ኢትዮጵያ የተረጋጋች ሆና ለተወሰነ ጊዜ ልትቀጥል ትችል ይሆናል፤ ነገር ግን ጠንካራ አትሆንም፡፡ በአብዛኞቹ ትንታኞች ዘንድ በቅርብ ጊዜ የሚነሳው ኢህአዴግን የመሳሰሉ ፖርቲዎች ሲወድቁ ከፍተኛ አቧራ ስለሚያስነሱ የሚፈጠረው ክፍተት ከፍተኛ ነው፤ በመሆኑም ተቃዋሚዎች “ሻዶ ገቨረንምነት” ማቋቋም እንዳለባቸው ይመክራል፡፡

አስተያየት ሰጪዎች “ አንድነትን” የመሳሰሉ ፓርቲዎች በተለይ በወታደራዊ ተቋሙ እና በአህኢዴግ ፓለቲካኞች ቀጣይ እጣ ፈንታ ላይ የተጠና አቋም መያዝ እንዳለባቸው ይመክራሉ፡፡ “እንቁላል በሁለቱ ጫፍና ጫፍ (በዋልታዎቹ) በመዳፍህ መካከል አይሰበርም ፤ በወገቡ በኩል በመዳፎችህ መካከል ከተጫንከው ግን ፍርክሽ ይላል፤ ኢህአዴግ ግዝፈቱን ስታየው እንቁላልን በዋልታዎቹ እንደመስበር ይከብዳል፤ የግዝፈቱ ለቁጥጥር ያለመመቸት ግን እንቁላልን በወገቡ እንደመስበር ቀላል ነው፡፡” ይላሉ ሙላቱ አርጋው፡
  

No comments:

Post a Comment