Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Wednesday, May 16, 2012

ከአልቃይዳና ከአልሸባብ ጋር ግንኙነት አላቸው የተባሉ ተጠርጣሪዎች ተከሰሱ

 By Ethiopian Reporter
በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በአሸባሪነት በተፈረጀው አልቃይዳና ራሱን አልሽባብ በማለት ከሚጠራው አሸባሪ ቡድን ጋር ግንኙነት አላቸው በሚል ተጠርጥረው በቁጥጥር ሥር ውለው በነበሩ አሥር ግለሰቦች ላይ የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ ትናንትና ክስ መሠረተባቸው፡፡ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት (ልደታ) ክስ የተመሠረተባቸው ተጠርጣሪዎች አንድ ኬንያዊና ዘጠኝ ኢትዮጵያውያን ሲሆኑ፣ ስድስቱ ኢትዮጵያውያን ክሱ የተመሠረተባቸው በሌሉበት ነው፡፡

ተጠርጣሪዎቹ ሐሰን ጃርሶ (የሚስጥር ስም አልሞሀጂሪን ናዚህአልሙ አቡሀ ሚልኪ አልቡራኒ) ኬንያዊ፣ መሐመድ ሀሽም (የሚስጥር ስም አብዱሰላም) ባሌ ዞን ሮቤ፣ ዑመር ሙሳ ኢሣቅ ባሌ ዞን ጉሮ ወረዳ እና አብዲ ሽኩር ዳውድ በማረሚያ ቤት ሆነው የተከሰሱ ሲሆኑ፣ የሱፍ ሐሰን፣ መሐመድ ሻፊ፣ አብዱራህማን ሁሴን፣ አብዱልለጢፍ አብዱራህማን፣ ከድር ሙስጠፋ፣ አብዲሳ ኡሲንና አብደላ ሁሴን የተባሉት ደግሞ በሌሉበት የተከሰሱ ናቸው፡፡

የዓቃቤ ሕግ የክስ ሰነድ እንደሚያስረዳው፣ ተጠርጣሪዎቹ የፖለቲካ፣ የሃይማኖት ወይም የርዕዮተ ዓለም (አይዲዎሎጂ) ዓላማን ለማራመድ በማሰብ፣ በመንግሥት ላይ ተፅዕኖ ለማድረስ ኅብረተሰቡን አስፈራርተዋል፡፡ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በአሸባሪነት ከተፈረጀው አልቃይዳና ራሱን አልሽባብ በማለት ከሚጠራው ቡድን ጋር አባል በመሆን የአገሪቱን መሠረታዊ ፖለቲካ ወይም ሕዝባዊ ተቋማትን ለማናጋትና ለማፈራረስ ተንቀሳቅሰዋል፡፡

ተከሳሾቹ ከ2000 ዓ.ም. መጨረሻ ጀምሮ ዋህቢያን እንደ ሽፋን በመጠቀም ጅሀድ ለመጀመር ሥልጠና በመውሰድና የጦር መሣርያ፣ የፈንጅና የከባድ መሣርያ አጠቃቀም ልምምድ በማድረግ፣ “የሙጂሀዲኖችና የአልሸባብ ንቅናቄ ካምፖች አስተዳደር” የሚል ፎረም በማዘጋጀት አባላትን መመልመላቸውን የዓቃቤ ሕግ ክስ ያስረዳል፡፡

የሃይማኖት ጦርነት ለማወጅ ሎጂስቲክና የሥልጠና ቦታ ለማዘጋጀት ገንዘብ እንዴት እንደሚገኝና የጦር መሣርያ ከጥቁር ገበያ እንዴት ማግኘት እንደሚችሉ፣ በውጭ አገር ከሚገኙ የአልቃይዳ አመራሮች ጋር በኢሜል ግንኙነት በማድረግ አመራር ይቀበሉ እንደነበርም በክሱ ተጠቅሷል፡፡

አንደኛ ተከሳሽና የኬንያ ዜጋ የሆነው ሐሰን ጃርሶ በ2001 ዓ.ም. ኬንያ ናይሮቢ ሳቢት በተባለ ሰው ተመልምሎ፣ “ሶማሊያ ውስጥ የሚገኙ የጅሀድ ወንድሞቻችንን ማገዝ አለብን” በማለት ከሌሎች ግብረ አበሮቹ ጋር ከተወያየ በኋላ፣ የጅሀድ እንቅስቃሴ ለማድረግ ወደ ሞቃዲሾና አዲወይን በመሄድ ከአልቃይዳ ታጣቂዎች ጋር መቀላቀሉን ክሱ ያብራራል፡፡

ተጠርጣሪው ሶማሊያ ውስጥ ከአልቃይዳ ታጣቂዎች ጋር በመቀላቀል ጋዛ በሚባል ማሠልጠኛ ውስጥ ከሚገኘውና ዜግነቱ ናይጄሪያዊ ከሆነው አካሽ ከሚባል የአልቃይዳ አመራር ጋር ከተገናኘ በኋላ፣ ከሌሎች አገሮች ከመጡ አሸባሪዎች ጋር በመሆን ለሦስት ወራት ልዩ ወታደራዊ ሥልጠና የወሰደና ውጊያ የተማረ መሆኑም በክሱ ተዘርዝሯል፡፡

በ2003 ዓ.ም. መጨረሻ የሽግግር መንግሥቱን ለመጠበቅ በሞቃዲሾ ከሚገኙ ከኡጋንዳና ከቡሩንዲ ከተላኩ የሰላም አስከባሪዎች ጋር ውጊያ ማድረጉም በክሱ ተካቷል፡፡

ተጠርጣሪው ሐሰተኛ የሆነ የኢትዮጵያ መታወቂያ አሠርቶ ወደ ኢትዮጵያ ከገባ በኋላ፣ ከመሐመድ ቃሲም (ሁለተኛ ተከሳሽ) እና ከዑመር ሙሳ (ከሦስተኛ ተከሳሽ) ጋር በመገናኘት፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን የጅሀድ እንቅስቃሴ ሁኔታ ሪፖርት ሲያደርግ መቆየቱም በክሱ ተጠቁሟል፡፡ አብዛኛዎቹ ተጠርጣሪዎችም ሞቃዲሾ በመሄድ የአልሸባብን ትምህርት የወሰዱ መሆናቸው ተገልጿል፡፡

በአጠቃላይ አንደኛ ተከሳሽ የአሸባሪውን ቡድን የሎጂስቲክስና የገንዘብ አሰባሰብ፣ የሥልጠና አመቻችና የጅሀድ እንቅስቃሴው በማስተባበርና በመምራት፣ ሁለተኛው ተከሳሽ ሰብሳቢና አመራር በመሆን፣ ሦስተኛው ተከሳሽ በውጭ አገር ያሉ የአሸባሪው ቡድን አባላት ተወካይ በመሆን፣ ስድስተኛው ተከሳሽ ደግሞ የሽብር ቡድኑ ሐሳብ አመንጪና ዕቅድ አውጭ በመሆን፣ ሁሉም በማስተባበሩና የቡድኑ የገቢ ምንጭ አመቻች በመሆን ሲንቀሳቀሱ የነበሩ መሆናቸውን የዓቃቤ ሕግ ክስ ያብራራል፡፡

ተጠርጣሪዎቹ የሽብርተኝነት ወንጀል ለመፈጸም ከግብረ አበራቸው ሻህ አረቡ ሳይድ ከሚባል ግለሰብ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አንዋር ንዑስ ቅርንጫፍና በተለያዩ ባንኮች ከአሸባሪ ቡድኑ ገንዘብ ሲላክላቸውና ሲቀበሉ እንደነበር በክሱ ተጠቅሶ፣ ሕግን በመጣስ ከሶማሊያ ወደ ኢትዮጵያ ግዛት በመግባትና በመውጣት ወንጀል መከሰሳቸው በችሎት ላይ ተነግሯል፡፡ ከአንድ እስከ አምስተኛ ያሉት ተጠርጣሪዎች በጠበቃቸው አማካይነት ክሱን የተቃወሙ በመሆኑ፣ ፍርድ ቤቱ ተቃውሞውን መርምሮ ብይን ለመስጠት ለነገ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡   

No comments:

Post a Comment