Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Thursday, May 3, 2012

ብአዴን አማርኛ ተናጋሪ የሕወሓት ክንፍ ወይስ የአማራው ወኪል?

 አንዳርጌ መስፍን ሽፈራው
እንደሚታወቀው ባለፉት 20 ዓመታት ውስጥ የአማራ ህዝብ ላይ እጅግ ዘግናኝና አሣፋሪ የሆኑ የጅምላ ግድያዎች ተካሂደውበታል፡፡ በመቶዎች የሚቆጠሩ አማራዎች እጆቻቸውና እግሮቻቸው የፊጥኝ እየታሰሩ እስከነ ሕይወታቸው በገደል ተጥለዋል፡፡ አሶሳ ላይ ስብሰባ ተብለው ተጠርተው ባንድ መጋዘን ውስጥ ከታጎሩ በኋላ በውጭ ተዘግቶባቸው በእሳት ተቃጥለዋል፡፡ በዚህ ሥልጡን ዘመን እንዲህ ዓይነት ዘግናኝ ግድያ በንፁሐን ዜጎች ላይ ይፈፀማል ተብሎ አይታሰብም፡፡ 

የአሰቦት ገዳም ደካማ መነኮሳት ሳይቀሩ ተገድለዋል፡፡ ጥቅምት 5 ቀን 1999 ዓ.ም የአቦ በአልን ለማክበር ከጅማ ከተማ 60 ኪ.ሜ ርቀት ላይ ባሻሽ አቦ በተባለ አካባቢ በአሮጊቶችና በሴቶች ላይ የተፈፀመው አሰቃቂ ግድያ(እርድ) ኃይማኖትን ሽፋን ያደረገ ቢመስልም የሥርዓቱን አስከፊነት ቁልጭ አድርጎ የሚያሣይ ነው፡፡ ካለፈው የካቲት ወር መገባደጃ ጀምሮ ከቤንች ማጂ ዞን ጉራፈርዳ ወረዳ በሺዎች የሚቆጠሩ አማራዎች ተባረው ርቃናቸውን አዲስ አበባ ሲገቡ አይተን አንጀታችን በሐዘን ተላውሷል፡፡ መጠጊያ አጥተው ላይ ታች ሲንከራተቱ ማየት ደግሞ ሌላው አሣዛኝ ገፅታ ነው፡፡ 

ከዚህ ሁሉ የከፋው ቤተክርስቲያን እንኳን ‹‹ከሞቀው ዘፋኝ›› ሆና ወይም በጎሳ አስተሳሰብ ታጥራ አላስጠጋም ማለቷ የእምነቱን አባቶች ጥያቄ ውስጥ ያስገባ ተግባር ሆኖ አልፏል፡፡ ይህንን በተመለከተ አንድ አዛውንት፡- “ድሮ ድሮ ቤተክርስቲያን እንኳንስ መጠጊያላጡ ዜጎች ይቅርና ወንጀል የፈፀሙ ወንጀለኞች ቤተክርስቲያን ገብተው ደውል በመደወል መንግሥት ምህረት እንዲያደርግላቸው ሲጠይቁ የሃይማኖት አባቶችም ያማልዱ ነበር፡፡ የዛሬዎቹ አባቶች ግን ደጀሰላምን ለመጠለያነትም እንኳ ከለከሉ” በማለት ቅሬታቸውን ገልፀዋል፡፡ 

አዛውንቱ እንዳሉት እነዚህ የዘመኑ የሃይማኖት አባቶች ዜጎችን በጭንቅ ጊዜ ቤተክርስቲያን እንዳይጠለሉ ሲከለክሉ ይህ የመጀመሪያ ጊዜያቸው አይደለም፡፡ በ1993 ዓ.ም የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች የመብት ጥያቄ ባነሱበት ወቅት የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ከግቢ አስወጥተው ሲያሳድዷቸው ቅድስት ማርያም ወርደው አባቶች ካሣዳጆቻቸው እንዲታደጓቸው ሲማፀኗቸው አሳልፈው መስጠታቸው አይዘነጋም፡፡ ከጉራፈርዳ የተሰደዱት ዜጎች እንዳረጋገጡት ድብደባና እንግልት ደርሶባቸዋል፡፡ ለምሳሌ አንድ ወጣት እየተደበደበ መኪና ላይ ቢጫንም በደረሰበት ድብደባ ተበሳጭቶ ከመኪናው ላይ ተወርውሮ ራሱን ፈጥፍጦ ገሏል፡፡

ዛሬ በኢትዮጵያ ውስጥ ፍትሕ ከመጥፋቱ የተነሳ ራሳቸውን በገመድ እያነቁ የሚገሉና ከላያቸው ላይ ቤንዚን እያርከፈከፉ ክብሪት እየጫሩ ተቃጥለው የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር እየተበራከተ መጥቷል፡፡ መምህር የኔሰው ገብሬ እስከ ጠ/ሚኒስትሩ ጽ/ቤት ድረስ አቤት ቢልም ሰሚ በማጣቱ ተበሳጭቶ ራሱንአቃጥሎ ሰማዕት ሆኗል፡፡ ካድሬዎችና ባለሥልጣናት ግን “አእምሮው ንክ ነበር” ሲሉ በከፈለው ዋጋ ተሳልቀውበታል፡፡ ጎንደርም አንድ መምህር እንዲሁ ፍትሕ አጥቶ ራሱን በገመድ ሰቅሎ ሲሞት “አእምሮ በሽተኛ ነበር” አሉት፡፡ ይህንን በተመለከተ አንዳንድ የስርአቱ ተቺዎች “ኢሕአዴግ አንድ ጊዜ ብቻ አይገልም፡፡ ከገደለ በኋላም የሟቾችን ታሪክ ጥላሸት ይቀባል” በማለት ይነቅፋሉ፡፡

አቶ ሽፈራው ሽጉጤም ዜጎችን ማፈናቀላቸው ሳያንስ ሚያዝያ 2 ቀን 2004 ዓ.ም በቴሌቪዥን ቀርበው፡- “አንድም አማራ አልተባረረም፡፡ 33 የሚሆኑ ብቻ ደን ስላቃጠሉ ተባረዋል” በማለት የሰጡት ማስተባበያ ራሱ ሕሊናን የሚያቆስል ነው፡፡ ይህንን ፕሮግራም የተከታተሉ አንድ የደቡብ ኢትዮጵያ ተወላጅ ግርምታቸውን እንዲህ ሲሉ ገልፀዋል ፡- “እነዚህን አማራዎች ለማባረር ሲባል ደኑ ላይ እሳት ለቀቁና እነሱ እንዳቃጠሉት ተቆጥሮ ለቴሌቪዥን እይታ አበቁት፡፡ ምነው እንግዲያው የእነሱ ቤት ሲቃጠል አላሳዩን? እሺ ይሁን እነሱ አቃጠሉት እንበል፤መቸም እነዚህ ዜጎች ሆነ ብለው ለጥፋት አያቃጥሉትም፡፡ በቆሎ ወይንም ማሽላ ለመዝራት ነው፡፡

 ታዲያ ለልማት ከሆነ ወንጀሉ ምኑ ላይ ነው?” በማለት ይጠይቁና “የደኑ መቃጠል ያየር መዛባትን የሚያስከትል ከሆነ የሕንድ፣የቻይናና የቱርክ ቱጃሮች የምዕራብ ኢትዮጵያን ደን በዘመናዊ ቡልዶዘር እየመነገሉ ምድረበዳ ሲያደርጉት ለምን ዝም ተባሉ? ታሪክ ይፍረደው!” ሲሉ በምሬት ተናግረዋል፡፡ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ “አንድም አማራ አልተባረረም” ይበሉ እንጂ አማራን ከደቡብ ክልል ጠራርጎ ለማስወጣት በወጣው እቅድ መሠረት እስከ 2006 ዓ.ም ድረስ 78 ሺ አማራዎች እንደሚባረሩ መረጃ አለ የሚሉ ወገኖችም አሉ፡፡

ሌላው አሳፋሪ ጉዳይ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ በጻፉት ደብዳቤ ላይ አባሪ ተደርጎ የተገኘዉ  ወረቀት “ወደ ሀገራችሁ ሂዱ” የሚል ሀይለ ቃል መገኘቱ ነው፡፡ ለመሆኑ ሰውየው እንዲህ ሲሉ ምን ማለታቸው ነው? መቼም ቢሆን አቶ ሽፈራውን የሚያህል ሰው የሀገርን ትርጉም አያውቅም ለማለት ይከብዳል፡፡ እሳቸውን ጨምሮ በኢህአዴግ ቋንቋ ሁላችንም ያለችን የብሔር ብሔረሰቦች አገር የሆነችው አንዲት ኢትዮጵያ ነች፡፡ ርግጥ ነው እያንዳንዱ ብሔር ብሔረሰብ፣የተወለደበት ቀዬ ወይንም እትብቱ የተቀበረበት የትውልድ ሥፍራ አለው፡፡ ችግሩ ግን አማራ በዚህ 20 ዓመት ውስጥ የሀገርም፣የክልልም፣የቀየም ባለቤት አለመሆኑ ነው፡፡ 

ስማቸውን እንዳልጠቅስ ያስጠነቁቁኝ አንድ ጎንደሬ፡- “አማራ በኢህአዴግ ዘመን ከማርስ እንደመጣ
ፍጡር መብረጃና መቋጫ በሌለው ሁኔታ ላይ ታች እየተዋከበ ማረፊያ ዛፍ ያጣ አሞራ ሆኗል፡፡ ተከዜን የሚያህል ዓለም አቀፍ ወንዝ ወሰን ሆኖ እያለ ጊዜ አገኘን ብለው ሰቲት  መራን፣ወልቃይት ጠገዴንና ማይፀምሪን ወደ ትግራይ ከለሏቸው፡፡ አማራውን ግን ከቀየው እያፈለሱት ነው፡፡ ይህም ሆኖ እንደ ሀገር አብረን እስከኖርን ድረስ ችግር የለውም፡፡ ችግሩ የሚመጣው የትግራይ ሪፐብሊክ የመሠረቱ እለት ነው፡፡ ያኔ ሆዱን ሞልቶ ተኝቶ የሚያድር አማራ አይኖርም፡፡

ሌላው አማራንና የኢትዮጵያን ሕዝብ የናቁበት ሁኔታ ነው፡፡ ለባህሪ መግዣ (ማባበያ) የመተማን ለም መሬት ለሱዳኖች እንደ አንባሻ እየቆረሱ መስጠታቸው ነው፡፡ ይህንን ውል የፈፀሙት ሚንስቴር ደረጃ ደርሰዋል” በማለት በቁጭት ተናግረዋል፡፡ ለመሆኑ በአማራ ላይ የበቀሉ ሁኔታ መነሻ ምክንያቱ ምንድን ነው? ለሚለው ጥያቄ አንዳንድ አማራዎች በግልጽ እንደሚናገሩት ከሆነ “ሕወሓት ገና ከመነሻው ጀምሮ ትግራይን ከኢትዮጵያ ገንጥሎ የትግራይን ሪፐብሊክ ለመመስረት ሲነሳ አማራን ቀንደኛ ጠላቱ አድርጎ ነው፡፡ ይህንንም በፋኖነት ዘመኑ ‘አማራ ገዳይ’ እያለ ተግብሮታል፡፡” ይላሉ፡፡ 

እኒሁ የአማራ ተቆርቋሪዎች “የሚገርመው ግን ዛሬም መንግሥት ሆኖ ከ21 ዓመት በኋላ እንኳን አማራን እየተከታተለ ከማሳደድ አለመቆጠቡ ነው፡፡ አማራ የጭንቅላት ካንሰር ሆኖበታል” ይላሉ፡፡
አንዳንድ የፖለቲካ ተንታኞች በበኩላቸው “ሕወሓት ወደ ሥልጣን ከመምጣቱ በፊትም ሆነ ከመጣ በኋላ በፈፀማቸው ጥፋቶችና በሚፈፅማቸው ስህተቶች ሁሉ የታሪክ ተጠያቂና ተወቃሽ ላለመሆን በአማራ ላይ ጣቱን ከመቀሰር ተቆጥቦ አያውቅም፡፡ ማባሪያ በሌለው የፕሮፖጋንዳ ዘመቻና የማፈናቀል ተግባር ተጠምዷል” ይላሉ፡፡ አንድ ስማቸው እንዲጠቀስ የማይፈልጉ ግለሰብ ደግሞ “ሕወሓት በሽብር ተፀንሶ በሽብር ተወልዶ፣የባሩድ ጪስ እያሻተተ ያደገ ፋኖ ድርጅት በመሆኑ በአእምሮው ውስጥ ሠላም አልተቀረፀበትም፡፡

 የተጠናወተው ጀብደኝነትና ማንአህሎኝነት ነው፡፡ በመሆኑም በማኅበረሰቡ ውስጥ የተረጋጋ ሠላም የለም፡፡ ሕወሓት የፋብሪካ ጭስ ከማየት ይልቅ የባሩድ ጭስ ማሽተትን ይናፍቀዋል፡፡ በዚህ 21 ዓመታት ውስጥ ሕዝቡ የሰቀቀን ኑሮ ነው የሚኖረው፡፡ ከሥራ መባረር፣ከመኖሪያ ቀዬ መፈናቀል በየእለቱ የምናያቸው ክስተቶች ናቸው፡፡ ሕወሓት/ኢህአዴግ ሥልጣን ላይ እስከ ቆየ ድረስም እነዚህ ሁኔታዎች ይቀጥላሉ” በማለት ቁጭታቸውን ይገልፃሉ፡፡ ሌላው አስተያየት ሰጪ በበኩላቸው፡- “ሕወሓት ኢትዮጵያን የባሕር በር ማሳጣቱንና ኤርትራን ተዋግቶ ማስገንጠሉን ሕጋዊና ፍትሐዊ ለማድረግ አንቀጽ 39ኝን በሕገ መንግሥት ቢቀርጽም የኢትዮጵያን ሕዝብ ይሁንታ ግን ማግኘት አልቻለም፡፡ 

በዚህ ምክንያትም አምባገንን ሆኗል፡፡ ሥልጣን አያያዙ በሕገወጥና በትጥቅ ትግል ነው፡፡ በኃይልና በመፈንቅለ መንግሥት የተያዘ ሥልጣን ደግሞ ሕጋዊነት ስለሌለው የተረጋጋ ሠላም የለውም፡፡ ሕወሓት/ኢህአዴግም ወይ የንጉሣውያን ደም አለኝ ብሎ ዙፋኑን አልወረሰ ወይ ዴሞክራት ነኝ ብሎ በመድበለ ፓርቲ ሥርዓት በምርጫ አሸንፎ ሥልጣን አልያዘ ወይ ለይቶለት ኮሚንስት ነኝ ብሎ የአንድ አምባገነን ፓርቲ ሥርዓት አልመሠረተ፤ እስከ መቼ እያምታታና ኮርጆ እየገለበጠ ይኖራል?” በማለት በትዝብት ይጠይቃሉ፡፡ እውነትም ኢህአዴግ እያምታታና እያተራመሰ የሚገዛበት ጊዜ ያበቃለት ይመስላል፡፡

 ሕጋዊነትን ለመላበስ ግን ሁለት ምርጫዎች ይኖሩታል፡፡አንደኛው የጭፍን የጥላቻ ፕሮፖጋንዳ እየነዛ አገሪቱን ቀውስ ውስጥ ከቶ መሞት፡፡ ሁለተኛው ነፃ ምርጫ አካሂዶ ካሸነፈ ሕጋዊ መንግሥት መሥርቶ በሥርዓት ማስተዳደር፤ ከተሸነፈም በሥርዓት ለአሸናፊው አካል አስረክቦ የታሪክ ባለቤት መሆን ነው፡፡ ከዚህ ውጭ ግን የሚፈጠረው አንዳንዶች “ሕወሓት ውሉ የጠፋበት ገና ከውጥኑ ‘የትግራይ ነፃ አውጭ ነኝ’ ብሎ በረሃ የገባ ጊዜ ነው፡፡ ኢትዮጵያን ከድቷታል፡፡ እንዴት ብሎ ነው የካዳትን ሀገር ሕጋዊ ሆኖ የሚገዛት? ዛሬ እንኳን ከዚህ አዙሪት ውስጥ አለመውጣቱ እንዳሸመቀ መሆኑ ይታወቅበታል” እንደሚሉት ነው፡፡

ሰሞኑን ከጉራፋርዳ የተባረሩትን አማራዎች በተመለከተ አንዳንድ የፖለቲካ ተንታኞች አፅንኦት ሰጥተው እንደሚናገሩት ከሆነ “ኢሕአዴግ በዘር ማፅዳት ወንጀል (ethnic cleansing) በዓለም አቀፍ ፍ/ቤት መከሰስ አለበት” ሲሉ ተደምጠዋል፡፡ የመኢአድ ፕሬዚዴንት ኢንጅነር ኃይሉ ሻወል ለፍኖተ ነፃነት ጋዜጣ 2ኛ ዓመት ቁጥር 38 እትም በሰጡት ቃለምልልስ “ከደቡብ ክልል ስለተፈናቀሉት ሰዎች የሚሉት ይኖራል?” ተብሎ ለቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ፡- ጉዳዩ የዘር ማጥፋት ዓላማ ያለው ነው፡፡በመሆኑም ከዓለም ዓቀፍ የሕግ ባለ ሙያዎች ጋር እየመከርንበት ነው” ብለዋል፡፡ 

አንድነት ለዴሞክራሲና ፍትህ ፓርቲ (አንድነት) በበኩሉ፡- “በዜጎቻችን ላይ እየደረሰ ያለው የማፈናቀል በደልን በማስመሰል ፕሮፓጋንዳ መደበቅ አይቻልም” በሚል ርእስ በሰጠው መግለጫ “የኢሕአዴግ የከፋፍለህ ግዛው የጎሳ ፖለቲካ ተግባራዊ መሆን ከጀመረበት 1983 ዓ.ም ጀምሮ በሀገራችን ተደጋጋሚ የሆኑ በደሎች ተፈጽመዋል፤ በበደኖ፣ በአርባጉጉ፣ በጉጂ፣ በወለጋ፣ በጋምቤላ፣ በሲዳማ፣ በተለይ በጌዲኦና በጉጂ ዞን የተፈፀሙ ግጭቶች የቅርብ ጊዜ አስከፊ ትዝታዎቻችን ናቸው” ይልና መግለጫው በመቀጠል “የደቡብ ክልል አስተዳደር በወሰደው ዜጎችን በኃይል የማፈናቀል ተግባር የሰው ሕይወት ጠፍቷል፣ ዜጎች በጦር ተወግተዋል፣ ለዓመታት የደከሙበትን ንብረት አጥተዋል. .. በዜጎች መፈናቀልና መሰቃየት ምክንያት የሆኑና መመሪያዎችን የሰጡ ባለሥልጣናት በሕግ መጠየቅ አለባቸው . . .” ብሏል፡፡ 

በመጨረሻም “ለመሆኑ ‹ለአማራ ሕዝብ መብትና ጥቅም የቆምኩ ነኝ› የሚለው ብአዴንስ ምን ይላል?” በማለት አንድነት ጠይቋል፡፡ አንድነት እንዳለው ለመሆኑ “የአማራው ሕዝብ ወኪል ነኝ” የሚለው ብአዴን ምን እየሠራ ነው? ብአዴንስ ማነው? የብዙዎች ጥያቄ ነው፡፡ ብአዴን ማነው? አልታደልንም እንጂ ሕዝብ የመሪዎቹን ማንነትና ምንነት የማወቅ መብት ነበረው፡፡ የኛ መሪዎች ግን እንኳንስ ማንነታቸውን ለሕዝብ ሊያስተዋውቁ ይቅርና ስማቸውን ሳይቀር ቀይረው ያሸመቁ ናቸው፡፡ ይህ ብቻ አይደለም የመጡበትን የዘር ግንድ ሳይቀር የደበቁና የቀየሩ ናቸው፡፡ ለማንኛውም የብአዴን ቁንጮ መሪዎች የሚከተሉት ናቸው፡-

1. አዲሱ ለገሠ (ኦቦ) የአሰበ ተፈሪ ልጅ ወይንም ተወላጅ
2. በረከት ስምዖን (መብራቱ) ጎንደር ተወልዶ ያደገ በእናቱም በአባቱም ኤርትራዊ
3. ተፈራ ዋልዋ የሀገር ማርያም ልጅ ወይንም ተወላጅ በአባቱ አማራ በናቱ ሲዳማ 
4. ታደሰ ካሣ (ጥንቅሹ) ኮረም ተወልዶ ያደገ በግማሽ ትግሬ በግማሽ አገው 
5. ካሳ ተክለ ብርሃን (ሸሪፎ) ሠቆጣ ተወልዶ ያደገ ትግሬና አገው
6. ሕላዊ ዮሴፍ (ቦግን) የአ.አ ልጅ ትግሬ ምናልባትም የኤርትራ ዘር ያለበት
7. ዮሴፍ ረታ (ገይድ ወይንም ዶሪ) የናዝሬት ልጅ ቤተሰቦቹ አርሲ
8. ተሠማ ገ/ሕይወት (የጎንደር ልጅ) ሙሉ በሙሉ ትግሬ (አድዋ)
9. ከበደ ጫኔ (ጣሣ) የራያ (ዋጃ) ልጅ ትግሬና አማራ
10. መለሠ ጥላሁን አርሲ ተወልዶ ያደገ ኦሮሞ
11. ኃይሌ ጥላሁን (ዘሪሁን) ሰሜን ሸዋ

እነዚህ ናቸው የብሔር አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ብአዴን) መሪዎች የነበሩት፡፡ ከላይ የተጠቀሱት ዜጎች ኢትዮጵያውያን ናቸው፡፡ እንደ ኢትዮጵያዉያንነታቸው የአማራን ሕዝብ የመምራትም ሆነ የማስተዳደር መብት አላቸው፡፡ ጥያቄው የሚነሳው ‹‹ሁልህም ወደ ወገንህ ሲባል አክንባሎም ወደ በረት፤ርኮት ወደ ቁርበት ተጠጉ›› እንደሚባለው ሁልህም በየክልልህ በገዛ ብሔረሰብህ ተዳደር ከተባለ መብቱን ለብሔሩ ተወላጅ መተው ነበረበት ነው ነቀፋው፡፡ ‹‹በቅሎ አባትሽ ማነው ቢሏት ፈረስ አጎቴ ነው አለች›› እንደሚባለው በአንድ ወቅት አቶ ታምራት ላይኔ (ጌታቸው ማሞ) ‹‹በእናቴ ወሎዬ በአባቴ ጎንደሬነኝ›› ብለው ነበር፡፡

 ኡጋዴን ወርደው ግን ‹‹ሽርጣም ይሏችሁ የነበሩትን ነፍጠኛ አማራዎችን አሳዩዋቸው. ..›› በማለት ንፁሀን ዜጎችን አስጨፍጭፈዋል ፡፡ ሌላው የብአዴን ከፍተኛ አመራር የሆኑት አቶ ተፈራ ዋለዋ በአንድ ወቅት ከቤንሻንጉል ጉሙዝ ወደ ዩኒቨርሲቲ ስለሚገቡ ተማሪዎች የኮታ አደላደል ጉዳይ ለሕዝቡ ለማስረዳት፣ እግረ መንገዳቸውንም ፖለቲካቸውን ‹‹ለመስራት›› ሰብስበው ‹‹ከክልሉ ብሔረሰቦች ተወላጅ ልጆች 2 ነጥብ ባልሞላ መግባት ይችላሉ. ..›› በማለት ሲናገሩ ‹‹እዚህ ተወልደው ያደጉት የአማራ ልጆችስ?›› ተብለው በሕዝቡ ሲጠየቁ ‹‹አማራውማ ድሮ ተምሯል›› በማለት የፌዝ መልስ ነበር የሰጡት፡ ፡ በተጨማሪም ‹‹ብአዴኖች›› የጎንደር መሬት ተቆርሶ ወደ ትግራይ ሲከለልም ትንፍሽ አላሉም፡፡ ለነገሩ ሊሉም አይችሉም፣ አማርኛ ተናጋሪ የሕወሓት ክንፍ ናቸውና፡፡

አንዳንድ የዋሀን “ብአዴን ምን እየሰራ ነው?” ብለው ለጠየቁት ጥያቄ ከበቂ በላይ መልስ የሚሆን ይመስለኛል፡፡ እውነት እንነጋገር ከተባለም ብአዴን አማርኛ ተናጋሪ የሕወሓት ክንፍ እንጂ አማራን አይወክልም፡፡ በ1983 ዓ.ም የሽግግር መንግሥቱ ጊዮን ሆቴል ላይ ሲመሠረት የሀገሪቱ ዜጎች ወኪሎቻቸውን ሲልኩ አማራ ወኪል አልነበረውም፡፡ እንዲልክም እድሉ አልተሰጠውም፡፡ በወቅቱ አቶ መለስ ዜናዊ “አማራ ወኪል የለውም፤ወደ ፊት ግን ተደራጅቶ እንደሚልክ ተስፋ አለን” ማለታቸው አይዘነጋም፡፡

በዚህ መሠረት በ1984 ዓ.ም መጋቢት ወር ላይ የመላው አማራ ሕዝብ ድርጅት (መአሕድ) ሲመሰረት እንደተለመደው ነበር ሕወሓት በቆረጣ የገባው፡፡ አዲስ ድርጅት እስከ ሚመሰርት ድረስ አላቆይ ብሎት ወደ አማራ ክልል እንደ መሸጋገሪያ ድልድይ የተጠቀመበት ሕብረ-ብሔራዊውን ድርጅት ሕዴንን አፍርሶ “ብአዴን” ብሎ በመሰየም ባሕርዳር ላይ አምባሻ ቆርሶ፣ፈንድሻ ረጭቶ “ከዛሬ ጀምሮ የአማራ ሕዝብ ወኪል ነህ” ብሎ መርቆ ለቀቀው፡፡ እንግዲህ ባጭሩ ብአዴን ማለት ይሄ ነው፡፡

Source: ፍኖተ ነፃነት ማክሰኞ ሚያዚያ 16 ቀን 2004 ዓ.ም

No comments:

Post a Comment