Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Saturday, December 1, 2012

አዲሱ የስልጣን ክፍፍልና አመክንዮው: (በዳዊት ተሾመ)

 እንደ መግቢያ
ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ ለረጅም ጊዜ ሲጠበቅ የነበረውን የካቢኒያቸውን ሽግሽግና አዲስ ተሿሚ ሚኒስትሮቻቸውን ትላንት (ህዳር 20፣ 2005 ዓ.ም) በፓርላማ በመገኘት አሹመዋል:: አዲሱ ካቢኔም ሶስት ም/ጠ/ሚኒስትሮች ሲኖሩት የአራት ሚኒስቴሮችን ሽግሽግም ያካተት ነው:: የቀድሞ ሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትር ሚኒሰቴር አቶ ጂነዲ ሳዶ ከሃላፊነት በማንሳት በአቶ ሙክታር ከድር ተተክተዋል:: የጤና ጠብቃ እና የንግድ ሚኒስትር ሚኒሰቴር ዲኤታ የነበሩት ዶ/ር ከሰተብርሃን አድማሱና አቶ ከበደ ጫኔ  እንደየቅደምተከትል ለሚመሯቸው ተቋሞች ሚኒስቴር ሆነዋል:: የጤና ጥበቃ ሚኒስትር ሆነው ሲያገለግሉ የነበሩት ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሀኖም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሆነው ተሹመዋል፡፡

 
በምክትል ጠቅላይ ሚኒስተር ማዕረግ የተሾሙት የሚከተሉት ናቸው:: ዶ/ር ደብረጽዮን ገብረ ሚካኤል የኢንፎርሜሽንና ኮሙዩኒኬሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር እና የፋይናንስና የኢኮኖሚ ዘርፍ አስተባባሪ፣ የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትሩ አቶ ሙክታር የመልካም አስተዳደር ማሻሻያ ዘርፍ አስተባባሪ እንዲሆኑ ሲደረግ በመስከረም ወር ከጠ/ሚ ሃይለማርያም ጋር የተሾሙት የትምህርት ሚኒስትር ሚኒሰቴሩ አቶ ደመቀ መኮንን የማኅበራዊ ዘርፍ አስተባባሪ  እንዲሆኑ ተሹመዋል::  በዚህም የተነሳ በምስራቅ አፍሪካ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ኢትዮጵያ ሶስት ም/ጠ/ሚኒስትሮች ይኖሯታል ማለት ነው::

አራቱ አመክንዮዎች
የዚህ ካቢኔ ሽግሽግ እና እንድምታው ብዙዎችን እያነጋገረ ነው:: አንዳንዶች ሁሉም ም/ጠ/ሚኒስትሮች በሚኒሰቴር ማዕረግ የሚመሯቸው ተቋሞች ስላሉ የታሰበውን የስራ ቅልጥፍና የሚያመጣ ሣይሆን አላስፈላጊ ቢሮክራሲ ማብዛት ነው ሲሉ ይሞግታሉ:: በአንድ በኩል ደግሞ የተወሰኑት አዲሱ የካቢኔ ሽግሽግ የብሄርሰቦችን እኩል የፌደራል ስልጣንተጋሪነት (Ethnic based balance of power at federal level)  በማረጋገጥ በፓርቲው ውስጥ ተከስቶ የነበረውን በተለይ ደግሞ የኦህዴድ ውስጣዊ ቀውስን ለማርገብ የታለመ ነው ይላሉ:: 

በሌላ በኩል ገዢው ፓርቲ በትጥቅ ትግል ወቅት ይከተል የነበረውን የጋራ አመራር (collective leadership) ባህል መልሶ ለመገንባትና እና በፓርቲው ልሂቃን ፊት ተደቅኖ ያለውን አስቸጋሪ ሁኔታ ለመሻገር የተነደፈ ፖለቲካዊ መፍትሄ ነው ብለው ይከራከራሉ:: ይህ የካቢኔ ሽግሽግ በህገ-መንግስቱ አንቀጽ 75 እና በ2003 ዓ.ም የአስፈጻሚ አካላትን እንደገና ለማደራጀት የወጣውን አዋጅ ቁጥር 691/2003 ክፍል ሁለት አንቀጽ ስድስት የተቀመጡትን ድንጋጌዎች የሚጣረስ መሆኑንና ህጋዊ እውቅና የሌለው መሆኑን የሚያመላክቱም አሉ::

በኔ አመለካከት ግን ከላይ የተጠቀሱት ምክንያቶች በተወሰነ ደረጃም ቢሆን የካቢኔ ሽግሽግን የሚገልጽ ቢሆንም፤ የስልጣን ሽግሽጉ መታየት ያለበት ሰፋ ባለ አተያይ መሆን አለበት ብዬ አምናለው:: ለምን አሁን ኢህአዴግ ሶስት ም/ጠ/ሚኒስትሮች እንዲኖሩ ፈቀደ? የሚለው መሰረታዊ ጥያቄ ነው:: ይህን መሰረታዊ ጥያቄ አራት መሰረታዊ ነገር ግን እርስ በራሳቸው በተወሰነ መልኩ በሚገናኙ አመክንዮች ሊመለስ ይችላል::

አንደኛ:-  የካቢኒው ሽግሽግ አንደኛው መገለጫ ሊሆን የሚችለው በፖለቲካ ትግል ተሸናፊ መስሎ የታየው ህወሃት ተንሰራርቶ የቀደሞውን የበላይነት  (Status quo) የመጠበቅ  በሌላ መልኩ ደግሞ አሸናፊ መስሎ የታየው ብአዴን ከአጥቂነት ወደ ተከላካይነት መውረድ ነው:: ይህ ምን ማለት ነው? የመስከረሙ 2003 የኢህአዴግ ሊቀመንበር እና ምክትል ሊቀመንበር  ምርጫ የተከናወነው  ህወሃት በመለስ ቦታ የራሱን ሊቀመንበር ከመምረጡ በፊት ነው:: በዚህም በሁለት መንገድ ብቸኛው ተጠቃሚ ሊሆን የሚችለው ብአዴን ነበር:: 

በእንድ በኩል የራሱን ሰው ምክትል ጠቅላይ ሚኒሰተር ሲያስደርግ በሌላ በኩል ደግሞ በቀላሉ ሊቆጣጠሩት የሚችሉትን፣ ፖለቲካዊ መሰረቱ፣ ወታደራዊ ድጋፉ እና አለምአቀፋዊ ተቀባይነቱ ብዙም የሌለውን የደኢህዴኑን ሃይለማርያም ጠቅላይ ሚኒስተር በማድረግ ነው:: ይህን የስልጣን ክፍፍል ተከትሎ ኦህዴዶች ቢያኮርፉም፣ መሰረታዊ የሆን የፖለቲካ ተጽእኖ ስለሌላቸው ህውሃት እራሱን አደራጅቶ አዲስ ፖለቲካዊ የስልጣን ሽግሽግን ለመፍጠር ለሚያደርገው ትግል ደጋፊ ሃይል ከመሆን የዘለለ ሚና አልነበራቸውም:: ህውሃት የራሱን መሪዎች ከመረጠ በኋላ እንደ አዲስ በተደረገው የስልጣን ሽግሽግ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስተርነት ማዕረግ የፋይናንስና የኢኮኖሚ ዘርፍ አስተባባሪነትና የውጭ ጉዳይ ሚኒስተርነት ሲደርሰው ኦህዴድም በምክትል ጠቅላይ ሚኒሰትርነት ማዕረግ የመልካም አስተዳደር ማሻሻያ ዘርፍ አስተባባሪነት ስልጣን ተቋዳሽ ለመሆን በቅቷል:: 

ማንም የዘመናዊ ኢትዮጵያን የፖለቲካ ታሪክ በቅርብ ለሚከታል ሰው ማንኛውም ቡድን (አጼ ሚኒሊክ፣ አጼ ሃይለስላሴ፣ ጓድ መንግሰቱ እና ጠ/ሚ መለስ እንዴት የስልጣን መድላድላቸውን እንዳደላደሉና ስልጣንን በብቸኝት እንደተቆናጠጡ ልብ ይሏል) የኢትዮጵያን የፖለቲካ ስልጣንን ለመቆጣጠር ከፈለገ በመጀመሪያ ደረጃ የመከላከያና ደህንነት፣ የኢኮኖሚ እንዲሁም የውጭ ጉዳይ ዘርፍን በበላይነት መቆጣጠር አለበት:: እነዚህ ዘርፎች አሁንም ቢሆን በድጋሚ በህውሃት ቁጥጥር ስር ነው ያሉት:: ስለዚህም አዲሱ የስልጣን ሽግሽግ የሶስቱን ዋና ዋና ብሄረሰቦች በፌደራል መንግስት የስልጣን ውክልና የሚያሳይ ነው የሚለው ብዙም የሚያሳምን አይደለም:: በተቃራኒው የስልጣን ድልድሉ ህውሃት የቀድሞውን ደረጃ ለመከላከል እንዲሁም የጠቅላይ ሚኒስትሩን እንቅስቃሴ በቅርብ ርቀት ለመቆጣጠር በሚችልበት ደረጃ ላይ መድረሱን የሚመላክት ነው::

ሁለተኛ:-  የአዲሱ የስልጣን ሽግሽግ ሁለተኛ አመክንዮ ሊሆን የሚችለው የኢህአዴግን ውስጣዊ ድርጅታዊ የስልጣን ሽኩቻዎችን ለጊዜውም ቢሆን እንኳን የሚያበረድ ሆኖ እንዲታይ መደረጉ ነው:: የአቶ መለስ ዜናዊን ሞት ተከትሎ በተደረገው የስልጣን ሽግግር በኢህአዴግ  በተለይ ደግሞ በኦህዴድ ውስጥ ከፍተኛ የስልጣን ሽኩቻና ቅሬታ ተነስቶ እንደነበር የሚታወስ ነው:: የህወሃትም ሆኑ የብአዴን ከፍተኛ ልሂቃን በኦህዴድ ውስጥ የተፈጠረውን የስልጣን ይገባኛልና ይህም የሚወልደውን ፖለቲካዊ ቅሬታ መፍታት የሚገደዱበት ምክንያት ያለኦህዴድ በኢህአዴግ ስም ማንኛቸውም ቢሆኑ ኢትዮጵያን የማሰተዳደር ቅቡልነት ስለማይኖራቸውና ለበለጠ ውስጣዊ መሰነጣጠቅ ስለሚያዳርጋቸው ነው:: ለዚህም አሁን በተደረገው የሥልጣን ድልድል የም/ጠ/ሚኒሰትርነትን እንደ እጅ መንሻ በመስጠት አራቱም ፓርቲዎች  የይምሰል  እኩል (pseudo equality) ፖለቲካዊ ሥልጣን ያላቸው በማስመሰል የተቀሰቀሰውን ሽኩቻ ወደ ከፋ ደረጃ ከመድረሱ በፊት ለመቀልበስ የተደረገ ፖለቲካዊ አካሄድ ነው:: 

ኦህዴዶች ሲያነሱ ለነበሩት የሥልጣን ይገባኛል ጥያቄ መልስ የሚሰጥ የሚመስል ነው:: በሌላም በኩል ህውሃት ባልተለመደ ምልኩ ከድርጅታዊ ሊቀመንበርነትና መንግስታዊ ጠቅላይ ሚኒስተርነት የስልጣን ድርሻ በአንዴ ገለል መደረጉ በመከላከያና ደህንነት አመራሮች የተፈጠረውን የመደናገጥና የመጠቃት ስሜት ለማስወገድም ጭምር ያለመ ሊሆን የሚችልበት ዕድል ሰፊ ነው::  ስለዚህም አዲሱ የካቢኔ ሽግሽግ የገዢውን ፓርቲ ውስጣዊ አንድነት እና መረጋጋት ሊያመጣ በሚያስችል መልኩ የተከናወነ ነው ብሎ መገመት ውሃ የሚያነሳ ሁለተኛው አመክንዮ ይሆናል::

ሶስተኛ:-  ጠ/ር መለስ ዜናዊ ስልጣን እንደተረከቡ ሙሉ በሙሉ በራሳቸው ቅጥጥር ስር የሆነ መንግስታዊ ስርአት ገንብተው ነበር ያለፉት:: የዚህ መንግስታዊ ስርአት የጎንዮሽም ሆነ የላይ ወደታች ግንኙነት በዋናነት እርስ በራሱ የሚጠባበቅና የሳቸውን የመጨረሻ ቃል የሚተገብር እንዲሆን ተደርጎ የተገነባ ነው:: በዚህ መንግስታዊ ስርአት ላይ በመለስ ዜናዊ ብቸኛ የሃሳብ አፍላቂነት የአብዮታዊ ዴሞክራሲና የልማታዊ መንግስት ጽንሰ-ሃሳብ  እንደ መንግስት ተልዕኮ ሲደረብበት የተመሰረተው መንግስታዊ ስርአት የበለጠ ውስብስብና በዚህም ምክንያት የተፈጠሩትን የተለያዩ ፍላጎቶች ካለሳቸው ውጭ የሚያቻችልና የሚያስታርቅ ሰው የሌለ አስመስሏል:: 

ለዚህ ዋነኛው ምስክሮች በተለያዩ ወቅት በኢቲቪ ብቅ እያሉ ስለሳቸው አስተያየተቸውን የሰጡት ከፍተኛ የመንግስት ሃላፊዎች ናቸው:: እንደነርሱ ከሆነ በእያንዳንዷ የፓርቲውና የመንግስት እንቅስቃሴ ላይ የሳቸው እጅ የጎላ ነበር ነው:: ይህም ማለት ካለመለስ ዜናዊ  የትኛውም የፓርቲ አመራር የመለስ ዜናዊን ቦታ ሊተካ ይቅርና በመለስ የተጀመሩትን ስራዎች የሚያስጨርስ አቅም ያለው የገዢው ፓርቲ አባል የሆነ ሰው የለም ማለት ነው:: ስለዚህ ከአንድ ብርቱ ሁለት መድሃኒቱ እንዲሉ እሳቸው ብቻቸውን ሲሰሯቸው የነበረውን እንቅስቃሴዎች በመከፋፈል ስራዎችን በተሳለጠና በተቀላጠፈ ሁኔታ ለማከናወን የተቀየስ ፖለቲካዊ ታክቲክ ሊሆን የሚችልበት ገጽታም አለው:: ስለዚህም የስራ ክፋፋልም ሌላው አመክንዮ ሊሆን ይችላል::

አራተኛ:-  ቀደምት የህውሃት አመራሮች ከሰሩት ታሪካዊ ስህተት የአሁኖቹ አመራሮች የተማሩና የእርምት እርምጃ የወሰዱበት አጋጣሚ ያለ ይመስለኛል:: ኢህአዴጎች ስልጣን እንደተቆናጠጡ ከጥቂት የማረጋጋት የስራ አመታት በኋላ ህወሃቶች ሁሉንም የፓርቲውንና የመንግስትን ሥራ ጠቅልለው  ለአቶ መለስ ዜናዊ በመተዋቸውና እነርሱ በሌሎች ግላዊ ጉዳዮች ላይ በማተኮራቸው በኋላ ላይ በውስጣቸው የተፈጠረውን ልዩነት በአቶ መለስ አሸናፊነት የተጠናቀቀበት አካሄድ ቁጭ ብሎ የሰቀሉት ቆሞ ለማውረድ ያስቸግራል የሚለውን ብሂል ያስታወሳቸው ይመስላል:: በተመሳሳይ መልኩ አዲሱ የስልጣን ሽግሽግ አቶ ሃይለማሪያም አቶ መለስ ያገኙትን ዕድል እንዳያገኙና የስልጣን ማዕከላዊነትን (centralization of power) እንዳያሰጠብቁ የታለመ የፖለቲካ ስትራተጂ ሊሆን የሚችልበት እድልም አለው:: ወትሮም ቢሆን አቶ ሃይለማሪያም ምክትል ጠ/ሚ እና ውጭ ጉዳይ ሚኒሰቴር ሆነው ሲሾሙ የአቶ መለስ ምክትልና  እና የአቶ ብርሃኔ ገ/ክርስቶስ አለቃ ነበር የሆኑት:: ምንም አንኳን አሁን ጠ/ሚ ቢሆኑም፣ አቶ ሃይለማሪያም በኢኮኖሚ፣ ዲፕሎማሲ፣ በመከላከያና በድህንነት መስክ በህውሃት የቅርብ ዕይታ ውስጥ ናቸው:: 

ስለዚም አዲሱ የካቢኔ ሽግሽግ የጋራ አመራር እንዲኖር ያስችላል የሚለው ሙግት ብዙም የሚያስኬድ አይደለም:: ምክንያቱም በም/ጠ/ሚ የተሾሙት ሁሉም የካቢኔ አባላት እንደመሆናቸው መጠን በመተጋገዝና በጉዳዮች ላይ እየተወያዩ በጋራ አመራር ለመስጠት የሚከለክላቸው ነገር የለም:: ከጋራ አመራር ከመስጠት ይልቅ ግለሰባዊ የበላይነት እንዳይነግስ ለመቆጣጠር እና የአንድ ሰው ፖለቲካዊ ስብእና ገዝፎ እንዳይወጣ በማድረግ የአንድ ሰው ፍጹም የበላይነትን ለመከላከል የተደረገ ፖለቲካ መፍትሄ ሊሆን የሚችልበት አመክንዩ የበለጠ የጎላ ነው:: በሌላ በኩልም ሲታይ የጠ/ሚ ሃይለማሪያምን ፖለቲካዊ ስብዕና እንዳይገዝፍ በማድረግ በቀጣይ ሊኖር በሚችለው የስልጣን ክፍፍል ላይ ህወሃት የጠ/ሚኒስትርነትን ቦታ የሚይዝበትን እድለ ለማመቻቸት የተነደፈ የፖለቲካ ስትራተጂ ሊሆንም የሚችልበት ዕድል ሰፊ ነው::

ማጠቃለያ
ከላይ የተጠቀሱት አመክንዮዎች በዋናነት የአዲሱን የሥልጣን ክፍፍልና የካቢኔ ሽግሽግ የተካሄደበትን ፖለቲካዊና ታሪካዊ(politico historical) ሁኔታዎችን ግምት ውስጥ በማስገባት ነው:: እንዚህ አመክንዮዎች እርስ በራሳቸው የሚደጋገፉም ቢመስሉም በተወሰነ ምልኩም እርስ በራሳቸው ሊጣረሱ የሚችሉበት አጋጣሚ አለ:: ሆኖም ግን ይህ ጸሃፊ እንደሚያምነው የዚህ የካቢኔ ሽግሽግ ፖለቲካዊ ግብ አንድ እና አንድ ነው ብሎ አያምንም:: ይልቁንም ተያያዥ የሆኑ ፖለቲካዊና አስተዳዳራዊ ግቦች ያለው ነው:: እንዚህን ግቦች ይህ ጸሃፊ ከተጠቀመበት የአተታይ ማዕቀፍ በተለየ መልኩ በማየት ከተለያዩ አቅጣጫዎች መመልከቱ ጉልህ አስተዋጽኦ አለው:: ይህውም፣ አዲሱን የስልጣን ሽግሽግ በመረዳት በተጨባጭ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን ፖለቲካዊ ነበራዊ ሁኔታ ለመቃኘትና የወደፊቱን የፖለቲካ ዕድገት ለማማተር የሚያስችል ይሆናል::

No comments:

Post a Comment