Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Wednesday, November 21, 2012

የመንግስት ጋዜጠኛው የሰራው የዜና ዘገባ ያለርሱ ፈቃድ ተቆራርጦ በቴሌቭዥን መቅረቡን አስታወቀ

ኢሳት ዜና:- የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ባልደረባ የሆነው ጋዜጠኛ አዲሱ መሸሻ በጠ/ሚኒስትሩ ጽ/ቤት ጥቅምት 23 ቀን 2005 ዓ.ም የተካሄደውንና ከፍተኛ ባለሥልጣናት የተሳተፉበት ውይይት አስመልክቶ በስፍራው በመገኘት ያጠናቀረው ፕሮግራም ያለአግባብ ተለውጦ እና ተቆራርጦ ለሕዝብ እንዲቀርብ መደረጉን አስታወቀ።

ሰንደቅ ጋዜጣ ይህንኑ አስመልክቶ ዛሬ እንደዘገበው፣ ጋዜጠኛ አዲሱ መንገሻ በዋናነት በመልካም አስተዳደር፣ በተጠያቂነት እና በሙስና ችግሮች ላይ ያተኮረውን ይህንኑ የስብሰባ ውሎ እንዲዘግብ ተመድቦ፣ ይህንኑ ውይይት በተመለከተ ከስድስት ደቂቃ በላይ የፈጀ የዜና ዘገባ ቢሰራም፣ ባላወቀው ምክኒያት እርሱ ያጠናቀረው ዜና ወደ ጎን ተትቶ፣ በስብሰባው ላይ በአካል ባልተገኘው ሌላ ባልደረባው የተሰራ ዜና ለሚድያ ፍጆታ መዋሉን አስታውቋል። 


ይኸው በጋዜጠኛ ሳሙዔል ከበደ የተከለሰው ፕሮግራምም ሆን ተብሎ የባለስልጣናቱ ሃሳቦች ተቆራርጠውነት ጥቅምት 27 ቀን 2005 ዓ.ም በኢትዮጵያ ቴሌቭዥን እንዲተላለፍ መደረጉንም ጋዜጠኛ አዲሱ ገልጿል።

ይህንኑ አስመልክቶ እየቀረበ ያለውን ቅሬታ በተመለከተ የተሰማውን ስሜት የገለፀው ጋዜጠኛ አዲሱ “የባለሥልጣናቱ ውይይት የመንግሥት አቋም እንጂ የግለሰብ አይደለም። ውይይቱን በአካል ተገኝቼ የተከታተልኩት ባለሙያ እያለሁ፣ ሳይነገረኝና ሳላውቅ ያዘጋጀሁት ፕሮግራም ተጥሎ፣ ተዛብቶና ተቆራርጦ እንዲቀርብ በመደረጉ ኃላፊነቱን መውሰድ ያለበት ጋዜጠኛ ሳሙኤል ከበደ እንጂ ተቋሙ አይደለም”ሲል አስታውቋል።

“አቶ ሣሙኤል ያልተከታተለውን ዝግጅት በራሱ ተነሳሽነት ብቻ ቆርጦ ያመጣል? ወይንስ እንዲያቀርብ የታዘዘው በበላይ ኃላፊዎች ቢሆንስ?” በሚል ለጋዜጠኛ አዲሱ ለቀረበለት ጥያቄ “ይህንንም ቢሆን እኔ እንዳውቀው መደረግ ነበረበት። በአለቆች ታዞ ከሆነ አዘውኝ ነው ማለት ነበረበት። በእውነትና ታዞ ከሆነ የተቋሙ ኃላፊዎች በዚህ ጉዳይ ላይ ኃላፊነት ሊወሰዱ ይገባል” ሲልምላሽ ሰጥቷል።

ጋዜጠኛ አዲሱ አያይዞም ይህን መሰል ችግር የሚፈጠረው በቢሮክራሲ ውስጥ ከኢሕአዴግ በላይ ኢሕአዴግ ነን የሚሉ ሰዎች በመኖራቸው ነው። በስብሰባው ውስጥ ተሳታፊ ከነበሩት መካከል ፕሮግራሙ እሁድ ባለመተላለፉ ቅሬታቸውን ለድርጅቱ ኃላፊዎች ማቅረባቸውንም ሰምቻለሁ ብሏል።

በሕዝብ ተወካዮች ምክርቤት ባለቤትነት በጠ/ሚኒስትሩ ቢሮ ጥቅምት 23 ቀን 2005 ዓ.ም የተካሄደው ስብሰባ በመልካምአስተዳደር፣ በተጠያቂነት፣ በሙስና ችግሮችና በመሳሰሉት ላይ ልዩ ትኩረት በመስጠት የተካሄደ ሲሆን በዚህ ውይይት ላይ የኢፌዲሪ ምክትል ጠ/ሚኒስትርና የትምህርት ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን ጨምሮ የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት አፈጉባኤ አቶ አባዱላ ገመዳ፣ በሚኒስትር ማዕረግ የስኳር ኮርፖሬሽን ዋና ዳይሬክተር አቶ አባይ ፀሐዬ፣ የመገናኛና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዶ/ር ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል፣ የእምባ ጠባቂ ተቋም ዋና እምባ ጠባቂ ወ/ሮ ፎዚያ አሚን፣ የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ዓሊ ሱሌይማን፣ የአ/አ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ አበባው ስጦታው እና ሌሎችም የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።

ይኸው ውይይት በኢትዮጵያ ራዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ሊተላለፍ ታቅዶ የነበረው ሰፋ ያለ ፕሮግራም በተያዘለት ዕለት ካለመተላለፉም በተጨማሪ በተላለፈበት ዕለትም ተቆራርጦ መቅረቡ፣ በአገራችን ውስጥ ዋነኛ አነጋጋሪ ጉዳዮች ሆነው ከሰነበቱት ጉዳዮች አንዱ ነው በማለት ባልደረባችን ቅዱስ ሀብት በላቸው ከአውስትራሊያ ዘግቧል።

No comments:

Post a Comment