Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Monday, September 10, 2012

እናንተ ወያኔዎች እንደ ቀትር እባብ መቅበዝበዛችሁን ትታችሁ እንደ ሰው አስቡ! ከፍቅሬ ዘለቀው



የአንባገነኖች ቁንጮና የዘረኞች መሀንድስ መለሰ ዜናዊ ሞት ነሐሴ 14፣ 2004 ዓ ም ይፋ ከተደረገ ጀምሮ የመንግሰቱ አቀንቃኞች፣ ደጋፊዎች፣ ሆድ አደሮች፣ ካድሬዎችና ሹማምንቶች ድንጋጤ ከመጠን ያለፈ ሆኖ እንደታየ ለመታዘብ በቅተናል። እውን ይህ ሁሉ ድንጋጤና መርበትበት እነሱ እንደሚሉት አገሩን የሚወድ፣ አርቆ አሳቢ፣ የልማት መሀንድስ፣ የአፍሪካ አባት፣ ኢየሱስ፣ ወዘተ… የሆነውን ንጉሳቸውን በማጣታቸው ነውን? መልሱ ግን አይደለም ነው። በሕዝብ አገልጋይነት ስም፣ በጌታቸው አጋፋሪነት የሕዝብን ንብረትና ሀብት በመዝረፍ ያገኙት የነበረው ጥቅም ሲቀር እየታያቸው እንጂ። 


በጣም የሚያሳዝነው ግን እነሱ ያዘኑትን ያህል፣ ይህን የተራበና በፍትህ እጦት የተሰቃየን የኢትዮጵያ ሕዝብ ከእነሱ ተርታ በግዳጅና በጥቅም አሰልፈው እንዲያለቅስ ማድረጋቸው ሳያንስ አላዘናችሁም፣ የእዝን መዋጮ አላዋጣችሁም፣ የመለስን ካኒታራ አልገዛችሁምና የመሳሰሉትን ምክንያቶች በመፍጠር ማሰቃየታቸው፣ መደብደባቸውና ወደ ዘብጥያ ማጋዛቸው ነው። ከዚህም አልፎ በአቶ መለስ ሞት የተደሰቱትን በስሜታዊነት መግደላቸው፣ በተለያዩ የዜና ማሰራጫዎች መዘገባቸው የቅርብ ጊዜ ትውስታችን ነው። 

የሀገሪቱ ርዕሰ-ብሔር ቢሞት አንድ የሀዘን ቀን ይታወጃል የሚለውንና ራሳቸው ያረቀቁትን ህገ-መንግሰት በመሻር ድፍን ሰማንያ ስምንት ሚሊዮን ሕዝብን ከሁለት ሳምንታት በላይ ከሥራ አግቶ፣ የቀድሞ መሪያቸውን ተክለ ሰውነት ለመገንባት ሲታክቱ መሰንበታቸው ለሀገርና ለህዝብ ደንታቢስነታቸውን ከማጉላቱም በላይ አቶ መለስ ከሌለ ሕዝቡን በብቃት መምራት የማይችሉ መሆናቸውን ምስክርነት መስጠታቸው እንደሆነ በሕዝባችን ዘንድ መነጋገሪያ ርዕስ ሆኖ የቆየ ቢሆንም እስካሁንም ትረካው ከኢትዮጵያ ቴሌቪዥን መስኮት  አለመጥፋቱ የሕዝብን የትኩረት አቅጣጫ ከውስጥ የስልጣን ሽኩቻና ችግሮቻቸው ለመቀየር መሆኑ እየታመነበት መጥቷል። 

ከዚህም ባሸገር የመማር ማስተማር ሂደቱን በማስትጓጎል መምህራንን በመሰብሰብ ከሁለት ሳምንታት ያላነሰ ስልጠና ሊሰጥ ሽር ጉድ እያሉ እንደሆነ ኢሳት በጳጉሜን 3፣ ዜናው ጠቁሞናል። የዚህ ሁለት ሳምንት የሥራ እገታ ውጤትና ለዚሁ ዓላማ የወጣው አለስፈላጊና የተሞለቀቁ ወጪዎች እንዲሁም ሌሎች ምክንያቶች ሳቢያ በአሁኑ ሰዓት ሕዝቡ በኑሮ ውድነት እየተጠበሰ ይገኛል። 

በአቶ መለስ ሀያ አንድ ዓመታት የግፍ አገዛዝ፣ የሕዝባችን የደም እንባ፣ ድንጋይ ተንተርሰው፣ ሲያገኙ ጥሬ ቆርጥመው፣ ሲያጡ ቅጠል በልተው ለሀገራችንና ለሕዝባችን እንዲሁም ለዓለም ደህንነት የሚፀልዩ የዋልድባ አባቶችና እናቶች መነኮሳት እሮሮ፣ የሙስሊም ወገኖቻችን ጥልቅ ሐዘን፣ ፅዋ ሞልቶ ተርፎ በመፍሰሱ ከእግዚያብሔር ፊት ደርሶ በደልን የማይረሳ ሀያል አምላክ ጊዜውን ጠብቆ ሁለት የአመፃ ከያኒያንን ከዚህ የባሰ በደል ሳያመጡ በሚል ዓይነት በሞት ቀጣ እንጂ ብዙሀኑ የኢትዮጵያ ሕዝብ ወይም በሌላ አነጋገር ተቃዋሚዎቻቸው ተጠያቂ አይሆኑም።

ታዲያ ይህ ሆኖ ሳለ በአቶ መለስ ረጅም የግፍ አገዛዝ ዘመናት የተገረፉትን፣ የተሰቃዩትን፣ የታሰሩትን፣ የተሳደዱትን፣ የተገደሉትንና የተፈጁትን ኢትዮጵያንን ለማስታወስና በአንባገነኑ ሞት የተሰማውን ደስታና በዚህም ሳቢያ ሀገራችን መልካም ነገር እንዲገጥማት ከወትሮው በበለጠ በቁርጠኝነት የነፃነታችን ባለቤት ለመሆን ቃል ለመግባት ተሞ በወጣው የዋሽንግተን ሰልፈኛ ኢትዮጵያዊያን ላይ ከፍትህና ከሀገር ጥቅም ይልቅ የግልና የዘረኝነት በሽታ የተጠናወታቸው በአሜሪካ የሚኖሩ የወያኔ ቅጥረኞች የሚያወርዱት የስድብ ውርጅብኝ በስነ ምግባርና በሐይማኖት ታንፆ በኢትዮጵያ ምድር ካደገ ጨዋ ህብረተሰብ የተገኙ ሳይሆን አሳዳጊ አጥተው ከጎዳና ላይ ተሰብስበው በስድብ ኮሌጅ ውስጥ ተመርቀው የወጡ ይመስሉ ነበር ሲሳደቡ። እጅግ አስነዋሪዎች ናቸው። 

እኔ በምኖርበት አገር ኖርዎይም በዚሁ ዕለት ማለትም አምባገነኑ መለስ ዜናዊ ይጠላት በነበረው መሬት ለአንዴና ለመጨረሻ ከነ ዘረኝነት ኮተቱ አፈር በሚለብስበትና ሌሎች ፍትህ ፈላጊ የዋሽንግቶንና ደቡብ አፍሪካ ሰልፈኞች ወንድሞቻችን በተሰለፉበት ነሐሴ 27፣ ቀን 2004 ዓ ም በተመሳሳይ ዓላማ በዲሞክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ ድጋፍ ድርጅት እና በኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ ኖርዎይ ቅርንጫፍ አስተባባሪነት ከኦስሎና አካባቢው ሰልፍ የወጣውን ኢትዮጵያዊ በተለመደው ዓይነት ተግባር ለመመረጅ ጥቂት የወያኔ አሸቃባጮች ውርውር ሲሉ ተስተውለዋል። ቀኑን ጥሩ ለብሰው የታዩትን ኢትዮጵያዊያንንም ከጌታቸው ሞት ስሜት ጋር በማያያዝ ሲሳደቡና ሲተናኮሉ ታይተዋል።  

በሀገሬ የፖለቲካና የደሞክራሲያዊ መብቴ ተጣሰ ብለው በሚኖሩበት አገር የፖለቲካ ጥገኝነት አግንተው ሳለ አሳደደን ላሉት መንግስት ድጋፍና የመረጃ ሥራ መስራት ዓለም አቀፍ የስደተኞች ህግን የመፃረር ወንጀል መሆኑን ዘንግተው አደባባይ ላይ በመውጣት አፀያፊ ሥራ መስራትና እንደቀትር እባብ ወዲያና ወዲህ ሲቅበዘበዙ መታየት አያዋጣምና እረጋ ብላችሁ ለሀገር ደህንነትና እድገት፣ ለሕዝብ ሰላም፣ ፍቅር፣ ፍትህና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ቅድሚያ በመስጠት እንደ ባለ አእምሮ ሰው ቆም ብላችሁ እንዲታስቡ እየመከርን ይህ ካልሆነ የግፉ ቀማሽ ከሆነው የኢትዮጵያ ሕዝብ መዳፍ ውስጥ ገብታችሁ ለሰራችሁት  መንጀል ተጠያቂ ከመሆን የማታመልጡ መሆኑን ልንነግራችሁ እንወዳለን። እግዚያብሔርም የማስተዋል ጥበብ ይሰጣችሁ ዘንድ እንለምናለን።

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

እግዚያብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቧን ይባርክ!!!

ጳጉሜን 4፣ 2004 (September 9, 2012), ለአስተያየት ፀሐፊውን በዚህ እሜል

ያገኙታል፡ belete_z@yahoo.co.uk

No comments:

Post a Comment