Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Friday, March 29, 2013

........እኔ የምለው ከክልል ወደ ክልል እየተንቀሳቀሱ ለመስራት እና ለመኖር ፓስ ፖርት እና ቪዛ ማስመታት ያስፈልገናል እንዴ? By ብሩክ ሲሳይ

እንደሚታወቀው ኢህአዴግ የሚባለው ገዢ ቡድን መንበረ ስልጣኑ ላይ ከወጣ ጀምሮ ብዙ አሳዛኝ ነገሮችን በህዝባችን እና በሀገራችን ላይ ሲፈፅም ቆይቷል አሁንም እየፈፀመ ይገኛል። ከነዚህ አሳዛኝ ነገሮች አንዱ እንደ አንድ ሀገር በአንድነት ለዘመናት ብዙ ርቀት የተጓዘን ህዝብ ወደ ኋላ በመመለስ የዘር እና ጎሳ ልዩነትን በሚያጎላ አካሄድ፤ ቋንቋን እና ዘርን መሰረት ያደረገ የከሸፈ የፌድራሊዝም አወቃቀር ስርዓት በመከተል እንደ ሀገር ብሄራዊ ስሜት እንዳይኖረን የክልል መንግስት የሚባል መዋቅር መፈጠሩ ነው። 

ሲመስለኝ ፌድራሊዝም በራሱ አስፈላጊ የሚሆነው እንደ ሀገር ተበታትነው በተለያየ አገዛዝ የነበሩ አካባቢወች ልዩነታቸውን በማቻቻል ወደ አንድነት መንግስት ለመምጣት ሲያስቡ እንደ መሸጋገሪያ ራስገዝ የሆነ የፌድራል ስርዓት ይመሰርታሉ፤ እነዚህን ራስ ገዝ ክልሎችም በበላይነት የሚመራና የሚቆጣጠር ከሁሉም አካባቢ የሚወከሉ አካላትን ያካተተ ማዕከላዊ መንግስት ይመሰረታል። ለዚህም ምሳሌ የሚሆነን ትናንሽ የተለያዩ መንግስታት የነበሩት የአሜሪካ ግዛቶች የፈጠሯት የዛሬዋ ዩናይትድ ስቴትስ ኦፍ አሜሪካ ነች። 


እንግዲህ አስቡት የአሜሪካ የተለያዩ ግዛቶች የነበራቸውን ልዩነት በማጥበብና የተሳካ ፌድራሊዝም አወቃቀር በመጠቀም አንድ ታላቅ ሀገር ሲመሰርቱ። በተቃራኒው የእኛወቹ ኢህአዴጎች ደግሞ በአንድነት ለዘመናት የቆየች ሀገርን የቋንቋንና ዘርን ልዩነት በማግነንና በማስፋት አንድ የነበረውን መንግስት ብትንትኑ ወጥቶ ወደ ብዙ ፌድራል መንግስታት ቀይሯል። የከሰረው መንግስታችን ለወደፊቱ ደግሞ እነዚህ የፌድራል ክልል መንግስታትነት ተገንጥለው ራሳቸውን የሚችሉ አገራት እንዲሆኑ ምቹ ሁኔታ በመፍጠር ላይ ይገኛል።

ታዲያ የፌድራሊዝም ሥርዓትን የሚከተሉት የተለያዩ የዓለማችን ሀገራት ምንም እንኳ በክልሎች የተከፋፈሉ ቢሆንም እያንዳንዱ ዜጋቸው ግን ሰርቶ ለመኖር በየትኛውም የአስተዳደራዊ ክልል እንደፈለገ መንቀሳቀስ ይችላል በመረጠው ቦታም ህይወቱን መምራት ይችላል። ወደኛ ሀገር ስንመጣ ህገ መንግስቱ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በኢትዮጵያ የግዛት ክልል ውስጥ የመንቀሳቀስና ሰርቶ የመኖር መብት አለው ቢልም በተግባር ግን እየታየ ያለው የዚህ ተቃራኒ ነው። ይሄን እንድል ያስገደደኝ ይህ መንግስት ወደ ስልጣን ከወጣበት ጊዜ ጀምሮ በግልፅ በአደባባይ በተለይ በተለይ አማርኛ ተናጋሪ ኢትዮጵያውያንን ለዘመናት ከኖሩበት ምናልባትም ከ 50 አመት በላይ፣ ተወልደው ካደጉበት፣ ንብረት ካፈሩበት ቦታ አስነስቶ ወደ አገራችሁ/ክልላችሁ ሂዱ በማለት ወደማያውቁት አካባቢ በግዳጅ፣ ንብረታቸውን እንዲበተን በማድረግ እያፈናቀለ ይገኛል። 

ቀደም ባሉት ጊዚያት በ80ዎቹ በሀረር፣ ባሌ፣ ወለጋ......አካባቢወች የሚገኙ አማርኛ ተናጋሪወች ላይ የተጀመረው የግድያና የማፈናቀል ሂደት አልፎ አልፎም ቢሆን በደቡብና ኦሮሚያ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ በተለያዩ ጊዚያት ተከናውኗል።ነገር ግን ከባለፈው አመት ጀምሮ ሰፋ ባለና በተደራጀ ሁኔታ እንደገና በቤንቺ ማጂ ዞን ጉራፈርዳ የሚኖሩ 50ሺህ በላይ አማርኛ ተናጋሪ ኢትዮጵያውያንን ከቦታው እንዲፀዱ የተደረገ ሲሆን በጣም አሳዛኙ ነገር ደግሞ እነዚህ ሰወች ያፈሩትን ሀብት ሳይሰበስቡ በግዳጅ በመኪና እየተጫኑ አዲስ አበባ ላይ መጣላቸው፣ ህፃናት ለጉዲፈቻ መዳረጋቸውና የጎዳና ተዳዳሪ መሆናቸው ነው። 

ይህ አማርኛ ተናጋሪዎችን የማፅዳት ዘመቻ ቀጥሎ በጅጅጋና በሀረር የተካሄደ ሲሆን በዚህ ወር ደግሞ ሰፋ ባለ አካሄድ በቤኒሻንጉል አካባቢ የሚገኙ አማርኛ ተናጋሪዎችን ማፈናቀሉ ቀጥሏል። ከሰሞኑ ደግሞ ከእስከ ዛሬው ሁኔታ በጣም ዘግናኝ የሆነ ድርጊት በወገኖቻችን ላይ የደረሰ ሲሆን ይሀውም እነዚህ ተፈናቃዮች በግዳጅ የተሳፈሩበት መኪና ተገልብጦ ከሾፌሩ ውጭ 59 ሰው ማለቁ ነው። በእውነት ልቤ በጣም አዝኗል!! ግን ይሄን የሚያደርጉት አካላት እንደኛው የሚያስብ ሰዋዊ አዕምሮ አላቸው? ምንድን ነው ከዚህ የሚያገኙት ትርፍ?

በእርግጥ የኢህአዴግ ቁንጮ የሆነው ህወሀት ገና የትጥቅ ትግል ሲጀምር ማንፌስቶው ላይ ካሰፈራቸው ነገሮች አንዱ አማራ ብለው የሚጠሩት ህዝብ መጥፋት እንዳለበትና ይህም ህዝብ ካልጠፋ የእነሱ ህልውና እንደማይኖር ያሳያል። ግን ያልገባቸው ነገር ህዝብ ይጠፋል ወይ? ምክንያቱስ ምንድን ነው? ለዘመናት አብረው የኖሩ ህዝቦችን ያኛው ካልጠፋ እኛ አንኖርም ማለቱ ተቀባይነትስ አለው ወይ? የሚጠፋው ህዝብስ ዝም ብሎ ያያል ወይ? (በእርግጥ ዝም ብሏል ነገር ግን ሁኔታወች መልካቸውን እየቀየሩ መሄዳቸውን እያስተዋልነ ነው;;) ከወረዳ ጀምሮ እስከ ፌደራል ድረስ ያላችሁ ይህንንስ ህዝብ እንወክላለን የምትሉ የገዥው ቡድን አስፈፃሚ ሎሌወች ለምን ብላችሁ የምትጠይቁት መች ይሆን? ትንሽ እንኳ አይቆረቁራችሁም? እስከ መቼ ነው በሆድና በውሸት የምትታለሉት? የሰው ልጅ እኮ ኢኮኖሚያዊ ፍጡር ብቻ አይደለም በገንዘብ የማይተመኑት ሞራል እና መንፈሳዊ እሴቶችም መገለጫወቹ ናቸው ታዲያ መቼ ይሆን የገዥው ቡድን ሎሌወች ሞራላዊ እና መንፈሳዊ ሰውነታችሁ የሚያዛችሁ? መቼ ይሆን ከራሳችሁ ወጥታችሁ ለብዙሀኑ የምታስቡት?

የገዥው ቡድን ከፍተኛ ሰወችና ሎሌወቻቸው ሥለ እነዚህ ተፈናቃይ ወገኖቻችን መፈናቀል መነሻ ምክንያት ምንድነው ተብለው ሲጠየቁ የሚሰጡት መልስ የተለመደ ውሸትና ማጭበርበር ከመሆኑም በላይ በንቀትና ሹፈት የተሞላ ነው፤ ብዙውን ጊዜ የሚሰጠው መልስም፦
1. ደን ስለሚያጠፉ ነው
2. በህገ ወጥ መንገድ ስለሰፈሩ ነው
3. ወንጀል ሰርተው ስለተሰደዱ ነው
4. የመኖሪያ ፍቃድ ስለሌላቸው ነው ወዘተ ይባላል

ነገር ግን እነዚህ መልሶች ሁሉም የማያሳምኑ እና የማያስኬዱ የተፈጠሩ የማምለጫ ውሸቶች ናቸው፤ ምክንያቱም ለምሳሌ ደን ጠፋ ወይም በህገወጥ መንግስት ሰፈሩ ከተባለ እነዚህ ሰወች አብዛኞቹ ይሄ ገዥ ቡድን ስልጣን ከመያዙ በፊት ለረዝም ዘመን በአካባቢው የነበሩ ናቸው ይሄ ገዥ ቡድን ስልጣን ከያዘ በኋላ እንኳ የተሰደዱ ቢኖሩ እስከዛሬ ለስንት አመታት ንብረት አፍርተው ሲኖሩ ምን እየተደረገ ነበር? እውነት ለደን የሚጨነቅ መንግስት ከሆነ በጋምቤላ፣ ቤኒሻንጉል፣ ሰሜን ጎንደር አካባቢወች በቻይና፣ ህንድና አረብ መሬት ተቀራማች ባለሀብቶች አማካኝነት ለእርሻ እየተባለ ከፍተኛ የደን ምንጠራ ሲከናወን መንግስት ለምን ዝም ይላል? 

በግሌ እነዚህ ተፈናቃይ ሰወች ደን መመንጠራቸውን አላውቅም? ቢመነጥርስ ይፈረድበታል እንዴ መሬቱ ለሱዳን ሲሰጥበት፣ መሬቱ ወደ ትግራይ ሲከለልበት፣ መሬቱ ወደ ቤኒሻንጉል ሲከለልበት ከጊዜ ጊዜ የመሬቱ መጠን እያነሰ ህዝቡ እየበዛ ሲሄድ ምን ማድረግ አለበት? የት ይሂድ? እንዲያውም እኮ መንግስት ነበር ለዚህ ችግሩ መፍትሄ መስጠት የነበረበት? ነገር ግን ከመንግስት ሳይጠብቅ በራሱ ጥሮ ግሮ ኑሮውን አሸንፎ ለኖረ እንደዚህ አይነት ግፍ ለምን ይደርስበታል? ሲያፈናቅሏቸው እንኳ ምናለ ንብረታቸውን እስኪሸጡ እና እስኪያደራጁ ጊዜ ቢሰጣቸው? ለምንስ ይዋከባሉ?

ወንጀል ሰርተው የተሰደዱ ናቸው የሚባል ከሆነ እውነት ይሄ ሁሉ ህዝብ ወንጀል እንዴት ይሰራል? ወንጀል ሰርተው ይሄን ያክል ዓመትስ ለምን ሳይከሰሱ ኖሩ? ወንጀል የሰራ ካለ ለምን ሳይፈናቀሉ ወንጀለኞች ወደ ፍርድ እንዲቀርቡ አይደረግም? እዚያ የተሰደዱበት ቦታ ተወልደው ያደጉት ህፃናትስ መብትስ አይከበርም ወይ? ደግሞስ አብዛኛወቹ በቀድሞወቹ መንግስታት የሄዱ ናቸው ወንጀል ከሰሩም ለምን በእነዚያ መንግስታት ለምን አልተከሰሱም? ወንጀል ከሰሩ ወንጀል የተሰራበት አካል የትአለና?????

ሌላው የመኖርያ ፍቃድ ስለሌላቸው ነው የሚባለው አስቂኝ ነው፤ ከክልል ወደ ክልል እየተንቀሳቀሱ ለመስራት እና ለመኖር ፓስ ፖርት እና ቪዛ ማስመታት ያስፈልገናል እንዴ? የመኖርያ ፍቃድ ያስፈልጋል እንዴ? ውጭ ሀገር አልሄዱ? አረቡ፣ ህንዱ፣ ቻይናው ከውጭ መጥቶ እንደፈለገው በሚፈልገው የኢትዮጵያ ክፍል ያሻውን እያደረገ ኢትዮጵያዊ ነኝ ብሎ የሚኮራው አማርኛ ተናጋሪ በሚፈልገው ቦታ ባደገበትና በተወለደበት ቦታ እንዳይኖር ማድረግ ምን ያክል ያስኬዳል? በጣም የሚገርመኝ ሁልጊዜም የሚፈናቀሉት አማርኛ ተናጋሪዎች ብቻ መሆናቸው ነው? ትግሬወች አይሰደዱም እንዴ? ቤንሻንጉል ትግሬ የለም? ኦሮሚያና ደቡብ ትግሬ የለም (እዚህ ላይ ትግሬወች በዚህ መንግስት እንደ ህዝብ ተጠቅመዋል የሚል ሀሳብ የለኝም)

.....ታዲያ ምነው አማርኛ ተናጋሪ ላይ ብቻ? ምን አደረገ አማርኛ ተናጋሪ? ኢትዮጵያን ስለሚወድ? አንድነትን ስለሚወድ? በእርግጥ በዚህ ስርዓት ኢትዮጵያን መውደድ ወንጀል ነው? በእውነት በዚች ሀገር ላይ መንግስት አለ ወይ? ለተበዳይ የሚቆም ሃይማኖታዊ ተቋም አለ ወይ???? ወዴት እየሄድን ነው? እንደው መንግስት ነኝ ከሚለው አካል እንዴት አንድ ሀላፊነት የሚሰማው ህሊና ያለው ሰው ይጠፋል?

No comments:

Post a Comment