Welcome!

"If you are neutral 0n the situations of injustice, You have choosen the side of oppressors." -Desmond tutu

Sunday, March 31, 2013

የመንግስትን ዘር ማፅዳት ዘመቻ ማስቆም የሁሉም ኢትዮጵያዊ ኃላፊነት ነው

ፍኖተ ነጻነት ርዕሰ አንቀጽ

አንባገነኑ የኢህአዴግ መንግስት የጻፈው ግን የማያነበው፣ አስከብረዋለሁ የሚለው ግን የማያከብረው የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ህገመንግስት በአንቀፅ 32 ማንኛውም ኢትዮጵያዊም ሆነ በህጋዊ መንገድ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚኖር የውጪ ዜጋ በነፃነት በመላ ሀገሪቱ የመንቀሳቀስ፣ የሚኖርበትን ቦታ የመምረጥ መብት እንዳለው ይደነግጋል፡፡


ሆኖም ኢህአዴግ አማርኛ ተናጋሪዎች በመረጡት አካባቢ የመኖር መብታቸውን ከልክሏቸዋል፡፡ ይህ አደገኛ የመንግስት አካሄድ በአፋጣኝ ካልቆመ በሀገራችንና በህዝቦቿ መልካም ግንኙነት ላይ የሚያደርሰው ጉዳት ከፍተኛ ነው፡፡  መንግስት እየፈፀመው ያለው ይሄ ዘመቻ አንድ ዘር ላይ ያነጣጠረ እንደነሆኑ ከዘር ማጥራት ተለይቶ ሊታይም አይችልም፡፡

የዘር ማፅዳት በአለም አቀፍ ደረጃ ከሚያስጠይቁ መንጀሎቹ መካከል ይጠቀሳል፡፡ በአለም አቀፍ ደረጃ እንደሚታወቀው በአንድ ቋንቋ ተናጋሪዎች፣ በአንድ ሃይማኖት ተከታዮች ላይ የሚደረግን ከአንድ ሀገር የማፈናቀልና የሰባአዊ መብት ጥሰት ማድረስን የሚጨምር ነው፡፡

ባለፈው አመት ከደብብ ክልል ሜንች ማጂ ዞን ጉራፈርዳ ወረዳ በሺዎች የሚቆጠሩ አማርኛ ተናጋሪዎችን ማባረር የጀመረው የኢህአዴግ መንግስት አሁን ደግሞ ከቤንሻንጉል ክልል በተለይም ከያሶ ወረዳ 25 ሺህ አማርኛ ተናጋሪዎችን ማባረር ተጀምሯል፡፡ በግዳጅ ለአመታት ከኖሩበት አካባቢ የሚባረሩት ዜጎች ድብደባ፣ ዝርፊያና ሌሎች ኢሰብአው ድርጊቶች የሚፈፀምባቸው ከመሆኑም በላይ በርካቶች ውድ ህይወታቸውን በማጣት ላይ ይገኛሉ፡፡

ዜጎቹ የሚባረሩበት ምክንያት የሚኖሩበት አካባቢ ተወላጅ አለመሆናቸው ነው፡፡ ለውጪ ባለሀብቶች ያለስስት ከአንድ ከተማ በላይ ስፋት ያለው ድንግል መሬት የሚሰጠው የኢህአዴግ መንግስት ኢትዮጵያውያንን “የትውልድ ስፍራችሁ አይደለም” በማለት በግፍ ማባረሩ ዛሬም ኢትዮጵያን የሚመሯት ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን ጥያቄ ምልክት ውስጥ እንድንከት የሚያስገድደን ሆኗል፡፡

ዜጎች በመረጡት የሀገራቸው ክፍል የመኖር ህገመንግስታዊ መብታቸውን በመነጠቃቸውና ህይወታቸውን እስከማጣት መድረሳቸው፣ ኢህአዴግ ለዘመናት ተዋዶና ተከባብሮ የኖረውን የኢትዮጵያ ህዝብ ለመነጣጠል የሚጠቀምበት እኩይ ስትራቴጂ መሆኑን አናጣውም፡፡ በዚህ ተግባሩ በኢህአዴግ የሚመራው የኢትዮጵያ መንግስትም ሆነ ባለስልጣናቱ ይዋል ይደር እንጂ በአለም አቀፉ ፍርድ ቤት መጠየቃቸው የማይቀር ነው፡፡

በተለይም ባሳለፍነው ሳምንት ከመኖሪያ ቀያቸው “ወደ ክልላችሁ ሂዱ“ ተብለው ሀብት ንብረታቸውን ጥለው ከተሸኙት ዜጎቻችን መሀከል 59 የሚሆኑት በመኪና አደጋ መሞታቸው በአካባቢው ነዋሪዎች ተረጋግጧል፡፡ መንግስት ሲያሳድዳቸው ህይወታቸውን ላጡ ዜጎች ልባዊ ሃዘናችንን እንገልፃለን፤ ለህይወት መጥፋቱ ግን መንግስት ሀላፊነቱን መውሰድ እንዳለበት እናምናለን፡፡ ያሟሟታቸውንም ሁኔታ የማጣራትና ለህዝብ የመግለፅ ግዴታውን እንዲወጣ ለማሳሰብ እንወዳለን፡፡

ሁሉም ኢትዮጵያዊ ህገመንግስታዊ መብቱን ተጠቅሞ መንግስት የጀመረውን የዘር ማፅዳት ዘመቻ የማስቆም ኃላፊነት አለበት፡፡ በተለይም የፖለቲካ ፓርቲዎችና የሲቪክ ማህበራት ከፍ ያለ ሸክም አለባቸው፡፡ እነዚህ ዜጎች የሚባረሩባቸው አካባቢዎች ያለው ህዝብም አጋርነቱን የማሳየት ግዴታ እንዳለበት እናምናለን፡፡

No comments:

Post a Comment